Tuesday, 1 November 2016

ሙሴ ተወለደ

ከሙሴ ፊት



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ከበረከት ጉዲሳ

ክፍል 1
የተወደዳችሁ የዳረጎት ዘተዋሕዶ ጦማር ተከታታዮች በመግቢያችን አንዳንድ ሃሳቦች ላይ ዉይይት አድርገን ነበር እነሆ ቀጣዩ
፩. ሙሴ  ከባርነት ያወጣቸው ህዝቦች እነማን ናቸው?
እስራኤላዊያን በግብፅ   
የእስራኤላዊያን የግብፅ የስደት ታሪክ የሚጀምረው እግዚአብሔር ስሙን ቀይሮ እስራኤል ካለው‹ ‹ነገስታትም ከጉልበትህ ይወጣሉ ለአብርሃምና ለይስሐቅ የሰጠኋትን ምድር ላንተ እሰጣለው  ከአንተም በኃላ ለዘርህ ምድሪቱን እሰጣለው››ዘፍ  34፡10-12 ብሎ ቃል ከገባለት   ከ ያዕቆብ እና  ከልጆቹ ነው፡፡  ያዕቆብ አስራ ሀለት ልጆች ነበሩት እነሱም ከልያ የተወለዱት  ሮቤል፣ስምዖን፣ሌዊ፣ይሁዳ፣ይሳኮር እና ዛብሎን ናቸው፡፡ ከራሔል የተወለዱት ደግሞ  ዮሴፍ እና ብንያም ናቸው፡፡ ከራሔል ባርያ ከ ባላ የተወለዱት  ዳን እና ንፍታሌም  ናቸው፡፡ እነዲሁም ከልያ ባርያ ከዘለፋ የተወለዱት  ደግሞ ጋድ እና አሴር ናቸው፡፡   ከእነሱ መካከልም ያዕቆብ በእርጅናው ወቅት የወለደው በመሆኑ አብልጦ የሚወደው ዮሴፍን ነው፡፡ ካለው ፍቅረም የተነሳ በብዙ ኅብር ያጌጠች ቀሚስም ከሌሎቹ ወንድሞቹ ለይቶ አድርጎለታል፡፡ በዚህም ወንድሞቹ ይጠሉት ስለነበር ከአባቱ ተልኮ ወደነሱ ዘንድ በመጣ ሰዓት ተመካክረው ለእስማኤላዊያን በ20 ብር ሸጡት እስማኤላዊያንም ወደ ግብፅ ወስደው በግብፅ ለፈርኦን ጃንደረባ ለዘበኞቹ አለቃ ለጴጢፋራ ሸጡት ዮሴፍም በጌታው ፊት ሞገስን ስላገኘ በቤቱ ሾመው ካለውም ሁሉ ሰጠው  ዮሴፍ መልከ-መልካም በመሆኑ የጌታው ሚስት ከሷ ጋር እንዲተኛ አስገደደችው ልብሱንም ተጠምጥማ ያዘች ዮሴፍ ግን ኃጢአት ላለመስራት እነዲሁም ጌታውን ላለመበደል ሲል ልብሱን ጥሎላት ትቷት ወጣ በዚህም  <ሊሳለቅብኝ ወደ እኔ ገባ>ብላ በሀሰት  ከሰሰቸው  ጌታውም በቁጣ ዮሴፍን ወደ ግዞት ቤት አስገባው፡፡ በዛም ሳለ በግዞት ቤቱ አለቃ ፊት ሞገስን አገኘ በዛው ሳለ በድለው ለመጡ ለፈርኦን የጠጅ አሳላፊ እና የእንጀራ አበዛ ህልምን ፈቶላቸዋል ይህም ህልም ፈቺነቱ ታውቆ ለፈርኦንም ሰባቱን የጥጋብ ዘመን እነዲሁም ሰባቱን የረሀብ ዘመን የፈታውም ዮሴፍ ነው፡፡ በዚህም ፈርኦን ዮሴፍን ‹ሁሉ ነገር እግዚአብሔር ላንተ ገልጾልሃልና ካንተ በቀር ብልህ የሚሆን ዓዋቂ ሰው  የለም በቤቴ ሁሉ አንተ ተሾም ሠራዊቴንም ሁሉ ለአንተ ቃል ይታዘዝ› ብሎ በግብፅ ምድር በሙሉ ተሾመ  ዮሴፍ በፈርኦን ፊት ሞገስን ከማግኘቱ የተነሳ የጣቱን ቀለበት አደረገለት ነጭ ሀርም አለበሰው የወርቅ ዝርግፍም አሠረለት ስሙንም እስፍንቶፎኔህ አለው ‹‹ወሰየሞ ሶሞ ፈርዖን ለዮሴፍ እስፍንቶፎኔህ››  ትርጓሜውም መዝገበ ኅቡአት ፣ ሊቀ ማእምራን ማለትነው አማርኛ ፍቺውም የአዋቂዎች አዋቂ ማለት ሲሆን በተለምዶ አራት አይና ይባላል፡፡  
የሰባቱ የድርቅ ዘመን በግብፅ አስቀድሞ ስለታወቀ በሰባቱ የጥጋብ ዘመን የተጠራቀመውን እህል በሰባቱ የረሀብ ዘመን ይሸጡ ነበር፡፡ በዚህም ያዕቆብ በግብፅ እህል እንዳለ ሰምቶ አስሩን ልጆቹን ወደ ግበፅ ላካቸው እህልም እንዲሸምቱ አዘዛቸው ብንያም ግን ከአባቱ ጋር ቀረ በግብፅ በደረሱ ሰዓትም ወንድማቸው ዮሴፍ አወቃቸው በመጀመሪያ ራሱን አልገለጠላቸውም ነበር በኃላ ግን እራሱን ገለጠላቸው አትዘኑም አላቸው በደስታም አቀፋቸው ‹‹እግዚአብሔር ሕየወትን ለማዳን ከእናንተ ፊት ሰዶኛልና›› አላቸው አባታቸውንና የቤትን ሰዎች ሁሉ ከብቶቻቸውንም ጭምር ይዘው ወደ ግብፅ እንዲመጡ ነገራቸውም በመጡም ሰዓት በጌሴም ተቀበላቸው
አሳረፋቸውም፡፡ ጌሴም በብሉይ ኪዳን መሰረት በታችናው (ሰሜናዊ) ግብፅ በአባይ ወንዝ አፍ ሠፈር ትገኛለች እስራኤላውያን በጌሴም 400 ዓመታትን ቆይተዋል፡፡ ጌሴም ራምሴም በመባል ትታወቃለች፡፡፡ እስራኤላዊያን ወደ ግብፅጌሴም ሲገቡ 70 ሆነው ነበር፡፡ (ዘፍ 37 -ዘፍ 50 )
ዮሴፍ የተሸጠው በ17 አመቱ ነው በፈርኦን ሲሾም 30 ዓመቱ ነበር ያረፈው 110 ዓመቱ ነው በሳጥን አድርገው ያኖሩትም  በዛው በግብፅ ነው፡፡ በግብፅ ዮሴፍን የሚጠላ ንጉስ ተነሳ ‹እነሆ የእስራኤል ልጆች ብዙ ጽኑ ሆኑ ይበረታቱብናል ፈፅመው በዝተዋል ከእኛም እነሱ ይፀናሉ ከጠላቶቻችን ጋር ሆነው ዕኛን ይወጉናል ካገራችንም ያስወጡናልና ኑ ብልሃት እንስራባቸው ጡብ እናስጥላቸው ጭቃ እናስረግጣቸው ኖራ እናስወቅጣቸው› አለ ብሎም አልቀረ መከራን ዕንዲያፀኑባቸው የሰራተኛ አለቆችን ሾመባቸው እስራአላውያን ግን መከራ ያጸኑባቸውን ያህል እንደ መከራው ብዛት እየበዙ እየጸኑ ነበር በዚህም አልበቃ ብሎ ንጉሱ ለዕብራዊያን ሴት አዋላጆች‹ ወንድ ከተወለደ ይገደል› ብሎ ትዕዛዝ ሰጠ ነገር ግን አዋለጆቹ እግዚአብሔርን ፈርተው የንጉሱን ትዕዛዝ ሳይፈፅሙ ቀሩ እስራኤላዊያንም ዳግም በአዋላጆች በጎነት በእግዚአብሔርም ቸርነት በዝተው በረቱ ዳግም ንጉሱ የተወለደ ወንድ ልጅ በውሀ ይጣል ብሎ አወጅ አወጣ
               በዚህ ጊዜ ለህዝቡ ተስፋ የሚሆን ሙሴ ተወለደ
 
አዲስ ዘመንና ቀመሩ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ዘመን የሚቆጠርበት፣ ቀመር የሚቀመርበት ትምህርት ባሕረ ሐሳብ ይባላል። ባሕረ ሐሳብ ከሁለት የግእዝ ቃላት የተገኘ ነው። ባሕር ማለት በዘይቤ ሳይሆን በምሥጢር ወይም በምሳሌው ዘመን ማለት ነው፤ “በመዳልው ደለወ ዓለመ በመሥፈርት ሠፈራ ለባሕር” እንዲል። ባሕርን ሰፈራት ይላል፤ ባሕር የሚሠፈር ሳሆን ባሕርን ዘምን ለማለትና ዘመን በአዕዋዳት የሚታወድ፣ በቀመር የሚቀመር፣ የሚሠፈር መሆኑን ለማሳየት ነው። ሐሳብ ማለት ፍችው ብዙ ቢሆንም  እዚህ ላይ በአጭሩ ቁጥር ማለት ነው። “ኢትትሐሰብሙ ወርቆሙ ወብሩሮሙ ወለጽድቅከኒ አልቦቱ ሐሳብ” (ለቸርነትህ ቁጥር ሥፍር የለውም) እንዲል አረጋዊ መንፈሳዊ፤ እንዲሁም ቅዱስ ዳዊት “ብፁዓን እለ ተኀድገ ሎሙ ኃጢአቶሙ ወእለ ኢሐሰበ ሎሙ ኵሎ ጌጋዮሙ” (ኃጢአታቸው የተተወላቸው፣ በደላቸው ያልተቆጠረባቸው ብፁዓን ናቸው) መዝ. 31፥1 ይላል። ስለዚህ ባሕረ ሐሳብ ማለት የዘመን አቆጣጠር ማለት ይሆናል። ሐሳበ ባሕርም ቢል ቁጥር ያለው ዘመን ማለት ነው። ኢትዮጵያውያን የዘመን አቆጣጠራቸውን፤ የበዓላትና የአጽዋማት አከባበራችን የሚመነጨው ከባሕረ ሐሳብ ነው።
የዘመን መለወጫ በመስከረም ስለመሆኑ
ሌሊቱ አልፎ ቀኑ ሲተካ ነጋ እንደምንል ክረምቱም አልፎ በጋው ሲተካ መስከረም ነጋ(ጠባ) እንላለን ይህም ከጨለማ ወደ ብርሃን ወጣን እንደማለት ነው። እንደዚሁም ሌሊቱን እንደምን አደራችሁ? ክረምቱን እንደምን ከረማችሁ? በማለትም ሰላምታ እንለዋወጣለን መልሱም እግዚአብሔር ይመስገን ብቻ ነው። ምክንያቱም ግርማ ሌሊቱን አሳልፎ ንፁህ አየርና ሰማይ ለማየት ላበቃን አምላክ ምስጋና ማቅረብ ተገቢ ስለሆነ ነው። መስከረም አሮጌው ዘመን አልፎ አዲሱ ዘመን የሚተካበት የወሮች መጀመሪያና የምድር ፍሬና የአደይ አበባ መታየት የሚጀምርበት ለፍጥረት ሁሉ አመች የሆነ የደስታ የተስፋና የበረከት ወር ነው። ስለዚህም ነቢዩ ዳዊት “በቸርነትህ ዘመን የተገኘውን እህሉን ታበዛዋለህ ተራሮች ልምላሜን አግኝተው ደስ ይሰኛሉ። የምድረ በዳ ተራሮችም በዝናብ ይረካሉ። ኮረብቶችም ደስ ብሏቸው ልምላሜውን እንደዝናር ይታጠቃሉ። የበግ አውሮች ስብን ይሰባሉ። ሸለቆዎችም እህልን ተሞልተው በደስታ ያመሰግናሉ ይዘምራሉ።” መዝ. 64፥11
መስከረም የዘመን መለወጫ ወርና ዕለት የሆነበት ምክንያት፤ ይሄውም የአዳም አስረኛ ትውልድ በሆነው በኖህ ዘመን የነበረው ማየ አይህ ከገፀ ምድር ጐድሎ ርግብ ለምለም ቅጠል ይዛ የመጣችበት እንዲሁም ኖህ ከመርከብ የወጣበት እግዚአብሔር አምላካችን በምድር ዘመን ሁሉ መዝራትና ማጨድ፣ ብርድና ሙቀት፣ በጋና ክረምት፣ ቀንና ሌሊት አያቋርጡም ብሎ ቃል ኪዳን የገባበት ስለሆነ ዓለም በዚህ ወር ይጀምር ነበረ (ዘፍ. 8፥8-22) ።
ሁለተኛም የኖህ ልጅ ካም ከወንድሞቹ ጋር ዕጣ በተጣጣሉ ጊዜ አፍሪካ ደረሰው ካም ወደዚህ ምድር የገባውም ልምላሜና አበባ ደምቆ አሸብርቆ በሚታይበት፣ ሌሊትና መዓልት በሚተካከሉበት በመስከረም ወር ነበር። እግዚአብሔር ለእስራኤል ነጻ የወጣችሁበት ወር የዓመት መጀመሪያ ይሁናችሁ እንዳላቸው ሁሉ (ዘጸ. 12፥2) የካም ልጆችም ይህንን ወደ ኢትዮጵያ የገቡበትን ወር የዓመት መጀመሪያ ይሁነን ብለው ርዕሰ ዓውደ ዓመት አድርገው ሰይመውታል (ኢሳ. 30፥29)።
እንቁጣጣሽ
እንጣጣሽ ልጆች ለወላጆች በአዲሱ ዓመት ዕለት የሚያቀርቡት የእንኳን አደረሳችሁ ገጸ በረከት ነው። ይኸውም ምሳሌ ዘፍ. 8፥8 በተጻፈው ታሪክ ላይ የተመሰረተ ነው። ርግብ የለመለመ የወይራ ቅጠል ይዛ ወደ ኖኅ ስለመጣች እጁን ዘርግቶ ተቀበላት ውሃም ከምድር እንደለቀቀ አወቀ ብሏል።
ሕጻናት እንደ የዋህ ርግብ ወላጆች እንደ ኖኅ ክረምት እንደ ማየ አይኅ በማድረግ ስጦታ ይሰጣሉ።
ሌላው ታሪክ ንግስተ ሳባ ለንጉሥ ሰሎሞን መቶ ሃያ መክሊተ ወርቅ እጅግም ብዙ ሽቱ የከበረ እንቈ ሰጠችው ይላል። (1ኛ ነገ 10፥10፣ 2ኛ ዜና 9፥9) ወርቅ እንቁ በፊቱ ስታቀርብለት “እንቋዕ እንቋዕ መጻእኪ ወለለ ዓመቱ ያምጽእኪ” (እንኳ እንኳ መጣሽ በየዓመቱ ያምጣሽ) ብሏት ነበርና የተከተሏት ወታደሮች በየዓመቱ እንቁጣጣሽ ይሏት ነበር።
ሁለተኛው ነጭ የወርቅ ፍልቃጭ የመሰለ ጥጥ ስለ አቀረበች እንቁ ጥጥ አመጣሽ ብሎ ነበር። ስለዚህ ነው። ሦስተኛም አበባ የመሰለ እንቁ ለጣትሽ ብሎ ነበርና በዚህ ተጠራ ይላሉ፡፡
አራተኛም በሉቃስ 1፥8 እንደ ተጻፈው ለዘካርያስ እጣ ደርሶለት ሲያገለግል መልአኩ ተገልጾለት የነገረውን ለኤልሳቤጥ ነግሯት ነበርና ስለዚህ “እንቁ እጣሽ” ተባለ።
ፍጻሜው ግን ለሔዋን ነው “እጸ በለስ መቁረጥሽ መብላትሽ ወደዚህ ዓለም መውረድሽ እንቁ ክርስቶስን ለማምጣት ነው ሲሉ እንቁጣጣሽ ተባለ ይላሉ። በግስ ዘይቤ ሲፈቱም ተንቆጠቆጠ፣ አንቆጠቆጠ በአረንጓዴ ቀጠል በነጭና በቀይ በቢጫ አደይ ወይም ጸደይ አበባ “ምድር ሆይ እግዚአብሔር አንቆጠቆጠሽ ወይም ዕንቡጥ አወጣሽ” በማለት ሊቃውንት ያብራራሉ።
ቅዱስ ዮሐንስ
ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ የመሸጋገሪያው ዕለት ቅዱስ ዮሐንስ ርዕሰ ዓውደ ዓመት ተብሎ ይጠራል። የካህኑ የዘካርያስ ልጅ መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ በዘመነ ሐዲስ መጀመሪያ ላይ ተነስቶ መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ እያለ ስለ ክርስቶስ አዳኝነት አስተማረ በየዓመቱ የዘመኑ መጀመሪያ ዕለት በእርሱ ስም ይጠራል።
በዚህ ዕለት ሕዝበ ክርስቲያኑ ሁሉ በአካባቢው ፀበል ወራጅ ወንዝ ይጠመቃሉ። ይኼውም ዮሐንስ “እኔስ ለንስሐ በውኃ አጠምቃችኋለሁ ጫማውን እሸከም ዘንድ የማይገባኝ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ግን ክእኔ ይልቅ ይበረታል፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስ በእሳትም ያጠምቃችኋል” ማቴ. 3፥12 የሚለውን ለማስታወስ ነው። ሁለተኛ ጻድቁ ኢዮብ በዮርዳኖስ ተጠምቆ ከአርባ ዓመት ደዌ ስለተፈወሰ ህዝቡም ከአሮጌው ዘመን ወደ አዲሱ ሲሻገር ከእድፉና ከኃጢአት ነፅቶ ዓውደ ዓመቱን ለማክበር ይጠመቃል (ስንክሳር መስከረም 1)።
ዘመናቱ በወንጌላውያን መሰየማቸው
በኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር እያንዳንዱ ዘመን በወንጌላውያን የተሰየመ የተጠራ ነው። የጌታችን የመድኃኒታችንን ቅዱስ ወንጌል የጻፉት አራት ወንጌላውያን ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስና ዮሐንስ ናቸው። ወንጌል ማለት የምሥራች ማለት ሲሆን በምድር ላይ ነግሦ የነበረው ሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ተወግዶ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስ መደረጉ፣ የሰው ልጅ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን መሸጋገሩ፣ ከዲያብሎስ ቁራኝነት ነፃ መውጣቱ የተነገረው በወንጌል ነው። ይህች ደገኛይቱ ሕግ የተባለችውን ወንጌልን አራቱ ወንጌላውያን በተለየ ቦታ በተለያየ ጊዜ ሆነው ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው በምሥጢር ሳይለያዩ ጽፈው ለእኛ አበርክተዋል። ለዚህ ውለታቸው የቀደሙት ቅዱሳን አባቶቻችን ዘመናት በስማቸው እንዲሰየሙ ደንግገዋል።
የዘመኑን ወንጌላዊ ለማወቅ 5500 ዓመተ ዓለምና ዓመተ ምሕረቱን ደምረን ለአራት ስናካፍል ቀሪው 1 ከሆነ ማቴዎስ፣ 2 ከሆነ ማርቆስ፣ 3 ከሆነ ሉቃስ፣ አልቦ (ዜሮ) ከሆነ ዮሐንስ ነው።
ከላይ እንደተመለከትነው አዲስ ዘመን የሚጀምረው መስከረም አንድ ቀን ሆኖ ይኸው በባሕረ ሐሳብ ዕለተ ቀመር ይባላል፤ ኢትዮጵያውያን ቁጥር የምንጀምርበት ስለሆነ ዕለተ ቀመር ተብሏል። ይህ ወቅት በደመና የተሸፈነው ምድር በጊሕ የሚተካበት፣ ብርሃን የሚፈነጥቅበት፣ ምድር አረንጓዴ ለብሳ ልምላሜዋ የሚታይበት የአትክልቱ መዓዛ የሚያውድበት ወቅት ነው።
በዚህም የተነሳ የሰው አእምሮ ይታደሳል ይለወጣል። በአዲስ መንፈስም ለሥራ የሚነሣሣበት ወቅት ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ በ1ኛ ጴጥ. 4፥3 ላይ “ያለፈው ዘመን ይበቃችኋል” የሚል ኃይለ ቃል አስቀምጧል። ከዚህ ኃይለ ቃል በርካታ ነገሮችን የምንማርበት ነው። አዲስ ዘመን ሲመጣ በዓል አክብሮ፣ ዘመኑን ቆጥሮ ማለፍ ብቻ ሳይሆን ካለፈው ዘመን የምንማራቸው ነገሮችን ለይተን ማስቀመጥና ጥሩ ሠርተን ያለፍነውን ማጠንከር፣ ያጐደልነውንና የደከምንበትን ጉዳይ ደግሞ የምናሻሽልበት የምንለውጥበትን መንገድ መቀየስ ይገባል። በተለይም በአዲስ ዘመን “ለዘኃለፈ ሥርየት ወለዘይመጽእ ዕቅበት” (ያለፈውን ይቅር በለን፤ በሚመጣው ይጠብቀን”) የምንልበት ሊሆን ይገባል። ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳስተማረው “የአሕዛብን ፈቃድ የፈጸማችሁበት ማለትም ዝሙትንና ምኞትን፣ ስካርንና ወድቆ ማደርን፣ ያለልክ መጠጣትንና ጣዖት ማምለክን ያደረጋችሁበት ዘመን ይበቃችኋል።” ባለው መሠረት ራሳችንን ለኃጢአት ያስገዛንበት ዘመን ከሆነ ለገቢረ ጽድቅ፤ በአምልኮተ ጣዖት የተያዝንበት ከሆነ ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር የምንመጣበትን፤ ነፍሳችንንም ሆነ ሥጋችንን አንጽተን ራሳችንን የምንለውጥበት ሊሆን ይገባል። አለበለዚያ ዘመኑ በላያችን ላይ እየተፈራረቀብን እየተቀየረ እኛ ግን በዚያ ቆመን በጠባይና ግብራችን የማንለውጥ ከሆነ ከንቱ ነው። እግዚአብሔር ይህን ዕድሜ የሰጠን ለንስሐ ነውና  ዘመኑ ሲለወጥ እኛም አብረን በንስሐ እየታጠብን በሐሳብ እየጐለመስን ልንለወጥ ይገባል።
እንግዲህ የክረምቱ ደመና ተወግዶ፣ ጨለማው ተገፎ በምትኩ ጎሕ የሚቀድበት፤ ብርሃን የሚፈነጥቅበት እንደሆነ እም በአሮጌው ዘመን በሕይወታችን ውስጥ ተጋርዶ የቆየውን ጨለማ አስወግደን ብሩሕ ተስፋ የምንሰንቅበት፣ አዲስ ዕቅድ አቅደን፣ የጐደለንን መሙላትና ድካማችንን በብርታት ማረም ይገባናል። ከዘመኑ ጋር አስተሳሰባችንን አመለካከታችንን ጭምር አብሮ መለወጥ አለበት።
አዲሱ ዘመን የሰላም፣ የብልፅግና፣ አዳዲስ ነገሮችን አቅደን እነዚህንም በመፈጸም ራሳችንን፣ ቤተክርስቲያናችንንና ሀገራችንን የምናሳድግበት የምንለውጥበት እንዲሆንልን የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ጸሎትና በረከት አይለየን።

ምንጭ፡ መዝሙረ ማኅሌት ወቅዳሴ በመምህር አፈወርቅ ተክሌ (የቅኔ መምህር) 2004 ዓ.ም የ2004ዓ.ም የመስቀል ደመራን በዓል አስመልክቶ በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የተዘጋጀ ልዩ ዕትም መጽሔት
http://www.sturaelmb.org/bereket.html

ሰማዕት ቅዱስ መርቆሬዎስ (ፒሉፓዴር)

ሰማዕት ቅዱስ መርቆሬዎስ (ፒሉፓዴር)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::
=>ለክርስትና ሃይማኖት የሚከፈል ትልቁ ዋጋ ሰማዕትነት ነውና ቤተ ክርስቲያን ለምስክሮቿ ሰማዕታት ልዩ ክብር አላት:: ከኮከብ ኮከብ እንዲበልጥ ሁሉ ከሰማዕታትም ቅዱስ ጊዮርጊስን እና ቅዱስ መርቆሬዎስን የመሰሉት ደግሞ ክብራቸው በእጅጉ የላቀ ነው::
+ቅዱስ መርቆሬዎስን ብዙ ጊዜ ሊቃውንት ካልዕ / ሁለተኛው ሊቀ ሰማዕታት ሲሉ ይገልጹታል:: ጥንተ ነገሩስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-
+በ2ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻ አካባቢ ከሮም ግዛቶች በአንዱ (አስሌጥ) ከአባቱና ከሚስቱ ጋር የሚኖር 'አሮስ' የሚሉት ሰው ይኖር ነበር:: ሚስቱ ደም ግባት የሠመረላት: እርሱም ደግነት ያለው ሰው ቢሆኑም የሚያመልኩት ግን ጣዖትን ነበር::
+አንድ ቀን አሮስ ሚስቱን ከቤት ትቶ ለአደን ከአባቱ ጋር ወጣ:: እንደ ልማዳቸው ወጥመዱን አስተካክለው ተደበቁ:: የወጥመዱ ደወል ሲያቃጭል: 'እንስሳ ተያዘልን' ብለው ሲሯሯጡ ዐይናቸው ያየው ነገር በድንጋጤ እንዲፈዙ አደረጋቸው:: 2 ገጻተ ከለባት በወጥመዱ ውስጥ ተይዘው ነበር::
+እነዚህ ፍጡራን ሰዎች ናቸው:: ግን ባልታወቀ የተፈጥሮ አጋጣሚ እንደዚህ እንደ ሆኑ ይታመናል:: ግን እጅግ ግዙፍ: ከአንገታቸው በላይ እንደ ውሻ: ወገባቸው እንደ ሰው: ጉልበታቸው እንደ አንበሳ ሲሆን ታችኛው እግራቸው የጋለ የናስ ብረት ነው የሚመስል::
+እነዚህን ፍጡራን ሰማያዊ ካልሆነ ምድራዊ ፍጡር አይችላቸውም:: አንበሳና ነብርን እንኩዋ እንደ ጨርቅ በጣጥሰው ይጥሏቸው እንደ ነበር ይነገራል:: ዐይናቸው እንደ እሳት ይነድ ስለ ነበር ማንም ትክ ብሎ ሊያያቸው አይችልም:: ምሥጢራቸውን ግን የሚያውቀው የፈጠራቸው አምላክ ነው::
+ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና:- አሮስና አባቱ ባዩአቸው ጊዜ ደንግጠው ወደቁ:: ገጻተ ከለባቱ የብረት ወጥመዱን እንደ ክር በጣጥሰው የአሮስን አባት በቅጽበት በሉት:: አሮስን ሊበሉት ሲሉ ግን ድንገት ቅዱስ መልአክ ወርዶ በእሳት ሰይፍ አጠራቸው::
+"ከእርሱ የሚወጣ ቅዱስ ፍሬ አለና እንዳትነኩት" አላቸው:: ወዲያውም መልአኩ ያንን ኃይለኝነታቸውን አጠፋው:: በዚህ ጊዜ 2ቱም ወደ አሮስ ሒደው ሰገዱለት:: አሮስም ወደ ቤቱ ወስዶም ደበቃቸውና የሆነውን ሁሉ ለሚስቱ ነገራት::
+ጥቂት ቆይታም ጸንሳ ወለደች:: ልጃቸውን ፒሉፓዴር (ፒሉፓተር) ሲሉ ስም አወጡለት:: ትርጉሙም "መፍቀሬ አብ-የአብ ወዳጅ" ማለት ነው:: ከዚያም አሮስ ሚስቱን ልጁንና 2ቱን ገጻተ ከለባት ይዞ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሒዶ ተጠመቀ::
+አበው ካህናት እሱን 'ኖኅ': ሚስቱን 'ታቦት': ልጁን ደግሞ 'መርቆሬዎስ' ሲሉ ሰየሟቸው:: መርቆሬዎስ ማለትም "ገብረ ኢየሱስ ክርስቶስ-የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ" እንደ ማለት ነው::
+ከዚያም ደስ እያላቸው: ክርስቶስን እያመለኩ: ነዳያንን እያሰቡ: ልጃቸውን መርቆሬዎስን አሳደጉ:: ነገር ግን የገጻተ ከለባት ወሬ በመሰማቱ ንጉሡ 'ካላመጣሃቸው' አለው:: ኖኅ ጸልዮ ወደ ኃይለኝነታቸው መልሷቸው ስለነበር ፊታቸው ገና ሲገለጥ ብዙ አሕዛብ በድንጋጤ ሞቱ::
+ንጉሡም ስለ ፈራ ኖኅን የጦር መኮንን አደረገው:: በጦርነት ጊዜም ገጻተ ከለባቱ ኃይላቸው ስለሚመለስ ተሸንፎ አያውቅም ነበር:: አንድ ጊዜ ግን 2ቱን ገጻተ ከለባት ንጉሡ አታሎ ወሰዳቸው:: ሃይማኖታቸውን ሊያስክዳቸው ሲል "እንቢ" በማለታቸው አንዱ ሲገደል ሌላኛው አምልጦ ጠፋ::
+በዚያ ወራትም ኖኅ ለጦርነት ወጥቶ ተማረከ:: ንጉሡ ደግሞ ታቦትን 'ላግባሽ' ስላላት የ5 ዓመት ልጇን ቅዱስ መርቆሬዎስን ይዛ ተሰደደች:: በስደት ጥቂት እንደ ቆየች ግን ባሏን ኖኅን አየችው::
+እርሷ ብታውቀውም እርሱ ዘንግቷት ነበር:: በሁዋላ ግን በሕጻኑ መርቆሬዎስ አማካኝነት ማስታወስ በመቻሉ ደስ አላቸው:: በዚያው በሮም ዙሪያ ሳሉም አንዱ ገጸ ከልብ መጥቶ አገኛቸው:: በዚህም ምክንያት በስደት ሃገርም መኮንን ሆኖ ተሾመ::
+በዚያም ቤተ ክርስቲያንን አንጾ: ቤቱን ቤተ ነዳያን አድርጐ ኖኅ ለዓመታት ኖረ:: ቅዱስ መርቆሬዎስ ወጣት ሲሆንም ወላጆቹ ታቦትና ኖኅ ዐረፉ:: እርሱ ከባልንጀራው ገጸ ከልብ ጋር ሆኖ በጾምና ጸሎት ሲኖር ስለ አባቱ ፈንታ የጦር መሪ አደረጉት::
+በጦርነትም እጅግ ኃያል: በሰው ዘንድም ፍጹም ተወዳጅ: የጾምና የጸሎት ሰው ሆነ:: ያን ጊዜ ግን ዳክዮስ ንጉሡ ክርስቶስን በመካዱ ምዕመናን ላይ ሞት ታወጀ:: በጊዜው ደግሞ የበርበር ሰዎች በሮም መንግስት ላይ ጦርነትን በማንሳታቸ ውዳኬዎስና ቅዱስ መርቆሬዎስ ለጦርነት ወጡ::
+ነገር ግን በርበሮች እንደ አሸዋ ፈሰው ብዛታቸውን ሲያይ ንጉሡ ደነገጠ:: ለማግስቱ ቀጠሮ ተይዞ ቅዱስ መርቆሬዎስ ሲጸልይ ቅዱስ ገብርኤል ወርዶ ሰይፍ ሰጠው::
+በማግስቱም 'ምን ይሻላል?' ሲባል ቅዱስ መርቆሬዎስ "እኔ የክርስቶስ ባሪያ ነኝና ብቻየን እቁዋቁዋማቸዋለሁ" ቢል ሳቁበት::
+እርሱ ግን በጥቁር ፈረሱ (አብሮት ያደገ ነው) ተጭኖ በርበሮችን "ጠብ ይቅርባችሁ: በሰላም ሒዱ" ቢላቸው ተሳለቁበት:: ያን ጊዜም ጸሎት አድርሶ የመልአኩን ሰይፍ ሲመዘው ብዙዎቹ ወደቁ:: ከበርበሮችም ለወሬ ነጋሪነት እንኩዋ የተረፈ ::
+ነገሩ በሮም ሲሰማ ታላቅ ሐሴት ሆነ:: ዳሩ ግን ከሃዲው ዳኬዎስ 'ድሉ የጣዖቶቼ የነ አዽሎን ነው' በማለቱ ቅዱስ መርቆሬዎስ ሲያዝን አደረ::
+በ3ኛው ቀንም 'ለጣዖት ሠዋ' የሚል ትዕዛዝ ከንጉሡ ዘንድ መጣ:: ቅዱሱ ግን ወደ አደባባይ ሔደ:: የክብር ልብሱንና መታጠቂያውን አውልቆ በንጉሡ ፊት ወረወረው::
+"ሃብትከ ወክብርከ ይኩንከ ለኃጉል: ሊተሰ ክብርየ ክርስቶስ ውዕቱ (ለእኔስ ክብሬ ክርስቶስ ነውና ንብረትህ ለጥፋት ይሁንህ)" ሲልም ንጉሡን በአደባባይ ዘለፈው:: ዳኬዎስም በቁጣ እሳት አስነድዶ: የብረት አልጋውንም አግሎ ቅዱስ መርቆሬዎስን በዚያ ላይ አስተኛው::
+ያም አልበቃ: ወታደሮች እየተፈራረቁ ሲደበድቡት ደሙ ፈሶ እሳቱን አጠፋው:: ለዚያ ነው ሊቃውንት:-
"አመ አንደዱ ላእሌከ ውሉደ መርገም:
እምቅሡፍ አባልከ እንተ ውኅዘ ደም:
አርአያ ዝናም ብዙኅ አጥፍኦ ለፍህም" ያሉት::
+ከዚያም ወስደው ወኅኒ ቤት ውስጥ ጣሉት:: ክርስቶስን ያስክደው ዘንድ በረሃብ: በግርፋት: በእሳት: በስለትም አሰቃየው:: በመጨረሻ ግን አሰቃይተው እንዲገድሉት ወደ እስያ ሰደደው:: በስፍራውም ብዙ አሰቃይተው ኅዳር 25 ቀን አንገቱን ሰይፈውታል::
+እርሱ ካረፈ በሁዋላም የተባረከ ፈረሱ ለዓመታት ወንጌልን ሰብኩዋል:: አረማውያንንም ከአፉ በወጣ እሳት አጥፍቷል:: ተአምረኛውና ኃያሉ ሰማዕት ቅዱስ መርቆሬዎስ በ200 ዓ/ም እንደ ተወለደ: በ220 ዓ/ም መከራ መቀበል እንደ ጀመረና በ225 ዓ/ም ሰማዕት እንደሆነ ይታመናል::
=>ሰማዕቱ በዚህች ዕለት በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ክርስቲያኖችን ያሰቃይና ይገድል የነበረውን ዑልያኖስን ያጠፋበት መታሠቢያ ይከበራል::
<<የቅዱሱ ክብር ታላቅ ነው>>
=>አምላከ ቅዱስ መርቆሬዎስ በከበረ ቃል ኪዳኑ ይጠብቀን:: ከርስቱም አያናውጠን:: ከበረከቱም ይክፈለን::
<ወስብሐት ለእግዚአብሔር>

“ በዚህች ዓመት ደግሞ ተዋት ” ሉቃ.13÷6-9

“ በዚህች ዓመት ደግሞ ተዋት ” ሉቃ.13÷6-9


ጌታችንና መድኃኒታችን ፈጣሪያችንና አምላካችን እግዚአብሔር ወልድ /ኢየሱስ ክርስቶስ/ በመዋዕለ ሥጋዌው በምሳሌ አድርጐ ወንጌልን አስተምሯል፡፡ በምሳሌ ማስተማር ሊተላለፍ የተፈለገውን መልእክት ሲያስተላልፉት ምግብን በጣፈጠ መረቅ ፈትፍቶ እንደ ማጉረስ ያህል ይሆናልና፤ እንዲሁም አንድ መልእከት በምሳሌ ጣፍጦ በቋንቋ ዘይቤ ተውቦ ሲቀርብ ምሥጢሩ ልብን  ይማርካል፡፡ ስለዚህ የሰው አእምሮ በሃይማኖት ልጓም ተስቦ ለምግባረ ጽድቅ እንዲዘጋጅ ጌታችን ለነጋዴው በወርቅ በዕንቁ፣ ለገበሬው በእርሻ በዘር፣ ለባልትና ባለሙያዎች በእርሾ በቡሆ፣…..ወዘተ እየመሰለ ያስተምር ነበር፡፡ማቴ.4÷30፡፡
እኛም ጌታ በምሳሌ ካስተማራቸው ትምህርቶች መካከል ለወቅቱ የሚስማማውን  መርጠን እንመለከታለን በሉቃ.13÷6-9 ላይ ይህንንም ምሳሌ መሰለ “ለአንድ ሰው በወይኑ አትክልት አጠገብ የተተከለች በለስ ነበረች ግን ፍሬ ሊፈልግባት ቢመጣ ምንም አላገኘም፡፡ ስለዚህ የወይን አትክልት ጠባቂዋን እነሆ ከዚህች በለስ ፍሬ ልፈልግ ሦስት ዓመት እየመጣሁ ምንም አላገኘሁምና ቁረጣት፤ ስለምን ደግሞ መሬቱን ታጐሳሉቁላለች? አለው፡፡” እርሱ ግን መልሶ ጌታሆይ ዙሪያዋን እስክኮተኩትላትና ፋንድያ እስካፈስላት ድረስ በዚህች ዓመት ደግሞ ተዋት፡፡ ወደፊት ግን ብታፈራ ደህናነው፤ ያለዚያ ግን ትቆርጣታለህ አለው፡፡”  ተብሎ ተጽፏል፡፡
ይህ ከላይ የተገለጸው ምሳሌ በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ሲተረጐም  /ሲመሰጠር/ እንዲህ ነው፤ የወይን አትክልት የተባለች ኢየሩሳሌም ናት፣ አንድ ሰው የተባለ እግዚአብሔር ነው፣ በለስ የተባሉ ደግሞ ቤተእስራኤል ናቸው፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ “እግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም ” ይላል ኢሳ.46÷25፡፡ ራሱ ጌታችንም “የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው፡፡ ” ብሏል ዮሐ.4÷35 ፡፡ ስለዚህ ሰማያዊያን መላእክትን እንዳይራቡ ያደረገ አምላክ እስራኤል ዘሥጋን ገበሬ በማያርስበት ዘር በሌለበት ዝናብ በማይጥልበት ምድረ በዳ መና ከሰማይ አውርዶ የመገበ ጌታ ተራበ ሲባል ያስገርማል! ግን ፍጹም አምላክ እንደ መሆኑ ፍጹም ሰው ሆኗልና አልተራበም አንልም፤ በሥጋ ተርቧልና የዕፀበለስ ፍሬን ፈለገ፡፡
ይኸውም የበለስ ውክልና ከተሰጣቸው ቤተ እስራኤል የሃይማኖትና የምግባር ፍሬን እንደፈለገ ያመለክታል፡፡ “በለስ ዘይቤ ቤተ እስራኤል እሙንቱ ”ተብሏልና እግዚአብሔር አምላክ በብሉይ ኪዳን በቅዱሳን ነቢያት አድሮ የሃይማኖት  /የምግባር/ ፍሬ ባገኝባቸው ብሎ ወደ እስራኤል ሔደ፤ ግን ምንም አላገኘም፡፡ እንዲያውም ሕዝቡ ቅዱሳን ነቢያትን በመጋዝ እየሰነጠቁ፣ በምሳር እየፈለጡ በማጥፋት ከዘመን ዘመን ወደ ተለያየ አዳዲስ ባዕድ አምልኮአቸው ሲገቡ አየ፡፡ ስለዚህ የበለስዋን ጠባቂ “ሦስት ዓመት እየመጣሁ ምንም ፍሬ አላገኘሁባትምና ቁረጣት” አለው፡፡ ሦስት ዓመት ያለው ዘመነ መሳፍንት፣ ዘመነ ነገሥታትና ዘመነ ካህናትን ነው፡፡ በዚህን ጊዜ የወይን ጠባቂዋ የተባለ መጋቤ ብሉይ ቅዱስ ሚካኤል “ተራድቼ ሥራ እስካሠራቸው ድረስ የዘንድሮ ይቅር በላቸው ” እያለ መለመኑን ያጠይቃል፡፡
አንድም ሰው የተባለ አብ ቢሉ በልጁ ህልው ሆኖ፣ ወልድ ቢሉ ሰው ሆኖ ሃይማኖት፣ ምግባር ፍለጋ ወደ እስራኤል ሄደ፡፡ ሦስት ዓመት በመዋዕለ ስብከቱ እየተመላለሰ ሲያስተምራቸውም ምንም ፍሬ አላፈሩምና “ይህችን ዕፀበለስ ቁረጣት ” አለው፡፡ መጋቤ ሐዲስ ቅዱስ ገብርኤል ግን “ ተራድቼ ሥራ እስካሠራቸው ድረስ ይቅር በላቸው፡፡ ”ብሎ ለመነ የጌታን ትምህርት ያልተቀበሉ አይሁድ ግን የንስሐ ንፍሬ ለማፍራት በጄ የሚሉ አልሆኑም፡፡ በአንደበታቸው የአብርሃም ልጆችነን ይላሉ፤ ነገር ግን የአብርሃምን ሥራ ሊሠሩ አልቻሉም፡፡ “ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል ልቡግን ከእኔ የራቀ ነው ” እንዲል፡፡
ስለዚህ ጌታ ከዕፀ በለሷ ዛፍ ምንም የሚበላ ፍሬ ስላላገኘ ረገማት፡፡ አንድም ጌታችን የፈለገውን ባለማግኘቱ ጉባኤ አይሁድን ረገመ፡፡  “በአንጻረ በለስ ረገማ ለኃጢአት ” እንዲል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ጉዳይ እስራኤል ከበረከት ይልቅ እርግማን እንዳገኛቸው አሕዛብ ደግሞ የእግዚአብሔርን ጸጋ እንዳገኙ ሲገልጽ “አሕዛብ በእግዚአብሔር ቸርነት አበባ ሰበሰቡ፤ በአይሁድ ዘንድ ግን እሾህ ተረፈ፡፡ ይኸውም የሃይማኖት ጉድለት ነው፡፡”ብሏል፡፡
ዛሬም ገበሬ ዘርን ዘርቶ አርሞና ኮትኩቶ ከአሳደገ በኋላ የድካሙን ፍሬ እንደ ሚጠብቅ ሁሉ፤ እግዚአብሔር አምላካችንም በድንቅ መግቦቱ ከአሳደገን ልጆቹ የምግባርና የሃይማኖት ፍሬን ይፈልግብናል፡፡ ግን ጌታ ወደ በለስ ሕይወታችን ቢመጣ ምን ያገኝ ይሆን? ፍሬ ወይስ ቅጠል? የእግዚአብሔር ቃል ግን ለንስሐ የሚገባውን ፍሬ እንድናፈራ ያዘናልና መንፈሳዊ ሕይወታችን እንዳይደክም፣ እንዳይጠወልግ፣ እንዳይደርቅና አላስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ደግሞ ወደ እሳት እንዳይጣል የንስሐን ፍሬ ልናፈራ ይገባናል፡፡ ሕይወት ያለ ንስሓ ክንፍ እንደ ሌላት ወፍ ናትና፡፡
በንስሓ ወደ እግዚአብሔር የሚመለሱ ሰዎች ግን ይቅርታን /ምሕረትን/ያገኛሉ፡፡ እግዚአብሔር የሚመለከተው ያለፈ ማንነታችንን ሳይሆን የዛሬውንና የወደፊቱን ሕይወታችንን ነውና፡፡ ቅዱስ ያሬድ “እግዚአብሔር ኃጢአታችንን በማሰብ እንጠፋ ዘንድ ከቶ አልተወንም ቸር አምላክ ነውና ” እንዲል፡፡ አዎ! እኛ በንስሓ ከተመለስን አምላካችን በኃጢአታችን ላይ አያስኬደንም፤ እርሱ የኃጢአታችንን አድራሻ ክረምት በፈለቀው ባሕር ውስጥ ይጥለዋልና፡፡ ሚክ.7÷18፡፡
እኛ ሰዎች ልብ ካልን በአዲሱ የዘመን መለወጫ ከተፈጥሮ እንኳ ብዙ ነገር መማር እንችላለን፡፡ አዝርእት፣ እፅዋት፣ ታድሰው፣ ቅጠላቸው ለምልሞ በአበባ ተንቆጥቁጠው እናያለን፡፡ ጋራ ሸንተረሩ አረንጓዴ ለብሶ፣ አፍላጋት በየቦታው እየተንፎለፎሉ፤ አዕዋፍ በዝማሬ፣ እንስሳት በቡረቃ ሰማይ ምድሩን ልዩ ያደርጉታል፡፡ ታዲያ ግዑዛኑ ፍጥረታት ጽጌ መዓዛቸውን የአዲስ ዓመት መሥዋዕት አድርገው ሲያቀርቡ እኛስ ምን ይዘናል?
ሰው ሠራሽ ሆኖ መዓዛ የሌለውን፣ ፍሬ የማያፈራውንና አበባ መሰሉን ሳይሆን፣ እግዚአብሔር የፈጠረውን፣ ያለመለመውንና አብቦ መልካም መዓዛ የሚሰጠውን የተፈጥሮ አበባን እንሁን፡፡ ያንጊዜ ዝንቦች ሳይሆኑ ንቦች ማርን ለማዘጋጀት ይቀስሙናል፡፡ ስለዚህ በሃይማኖት ብቻ ያይደለ በምግባርም እናብብ፡፡ ያን ጊዜ ከዘማሪው ክቡር ዳዊት ጋር “በቸርነትህ ዓመታትን ታቀዳጃለህ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል የምድረ በዳ ተራራሮችም ይረካሉ ” ብለን ለመዘመር እንበቃለን ፡፡ መዝ.64÷11-13፡፡
በአጠቃላይ አዲስ ዘመን የአምላክ ስጦታ /በረከት/ ነው፡፡ ስለዚህ በምድር ላይ የሚኖር ማንኛውም ሰው ዘመኑ በፈጣሪ ምልጣን የተያዘና የተገደበ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ እኛ አፈር እንደሆንን አስብ፤ ሰው ዘመኑ እንደ ሣር ነው፡፡ እንደ ዱር አበባም ያብባል ነፋስ በነፈሰበት ጊዜ ግን ያልፋል ” በማለት ሰው ካደገ በኋላ በሕመም ፀሐይነት ይደርቅና በሞት ነፋስነት ይወሰዳል፡፡ ባለፈው ዓመት ብዙዎች ወደ ሞት መንደር ደርሰዋል፤ እኛም እንደ ነርሱ መንገደኞች መሆናችንን እንርሳ፡፡
ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስም በበኩሉ“ ሣሩ ይደርቃል፤ አበባውም ይረግፋል፤ የአምላካችን የእግዚአብሔር ቃል ግን ለዘለዓለም ጸንቶ ይኖራል ” በማለት የሰው ሁሉ ክብሩ ሥጋዊ ሕይወቱና ተድላ ደስታው አንድ ጊዜ፣ አንድ ወቅት ለምልሞና አምሮ የሚታይ ሆኖ ሳለ ያው ደግሞ ሳይቆይ የሚጠፋ መሆኑን ያመለክታል፡፡ ኢሳ.40÷8፡፡ ስለዚህ በአዲሱ ዘመን ራሳቸውን ለከፍተኛ ግብ የሚያዘጋጁ ሁሉ ወደ ተቀደሰ መንፈሳዊ ሕይወት ሊሸጋገሩ ይገባል፡፡ ከእግዚአብሔር የተሰጠን እድሜም የአጭር ጊዜ እንግዳ መሆናችንን ስለሚያስገነዝበን የምንሸኘውም እንዲሁ ባልታወቀ ጊዜው ስጥ መሆኑን በመረዳት እውነተኛ ሃሳባችንና ሥራችንን ለተተኪው ትውልድ የማይረሳ አስመስጋኝ ቅርስ መሆን አለበት ፡፡
እንዲህ ዓይነቱ መልካምነት ደግሞ ለክርስቲያን በአዲሱ ዘመን እንደ ሎተሪ ዕጣ የሚደርሰው ሳይሆን ራሱ ፈልጐ የሚሆነው ነው፡፡ ስለዚህ ይልቁንም በአሁኑ ዘመን በመጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው ሁሉ ፍጻሜ እያገኘ ባለበት ዘመን ፍቅር በጠፋበት ዘመን አብዛኛው ሕዝብ ለማይረባ ነገር ብሎ ደገኛ ሃይማኖቱን እየለቀቀ ወደ አልባሌ ቦታ ሲገባ የሕይወት ለውጥ ማምጣት ያስፈልጋል፡፡ እኛ በአዲሱ ዓመት የሕይወት ለውጥን ካሳየን የእግዚአብሔር ጸጋ በውስጣችን ሥራውን በመጀመር በአንድ ሰንሰለት ላይ በርካታ የሕይወት ለውጥን ያመጣልናል፡፡ ይህ የሕይወት ለውጥ በአዲሱ ዘመን ውስጥ ለመኖሩ ተግባራዊ መለኪያው ደግሞ ቀጣይነቱ፣ ፍጹም ተጋድሎውና ግልጽ መሆኑ ነውና ራሳችንን እንመርምር፡፡ 1ጢሞ.4÷7፡፡
የዚያች የወይን ጠባቂ  “ ወደ ፊት ብታፈራ ደህና ነው ያለ በለዚያ ግን ትቆርጣታለህ ” እንዳለ ለነፍሳችን አንድ ነገር ሳንይዝ፣ ዘመናችን እንዳያረጅና እንዳይቆረጥ ዛሬ ለበጐ ሥራ እነነሣ፡፡ መጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አሁንም “ምሳር በዛፎች ሥር ተቀምጧል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል ” ይላልና፡፡ ማቴ.3÷10 እነሆ ! ዛሬ ግን እንደ እግዚአብሔር ቸርነት አሮጌውን ዓመት አሳልፈን ለአዲሱ ዓመት በቅተናል፡፡ ስለዚህ አዲሱን ዓመት በመንፈሳዊ ሕይወታችን ጐልምሰን ፣ ሁላችንም ለተቀደሰ ዓላማ ተሰልፈን፣ ከክፉ ምግባራችንም ተመልሰን የምንቀደስበት የምንባረክበት የሰላም፣ የጤናና የደስታ ዘመን ያድርግልን አሜን!!

ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት

ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት


ሐምሌ አሥራ ዘጠኝ ቅዱስ ገብርኤል የራማው ልዑል ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ሕጻኑ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ከሚነደው እቶን እሳት ያዳነበት ዕለት ነው፡፡ ይህ ቀን ለክርስቲያን ሁሉ የተድላ የፍስሐ በዓል ነው፡፡ የጌታችንን ምሕረትና ቸርነት የመላአኩን አዳኝነት ተራዳኢነት ያየንበት ዕለት ነው፡፡ እኛም ለዕለቱ የሚስማማውን ትምህርት ይዘን ቀርበናል መልካም ንባብ
ሦስት ዓመት እንኳን ሳይሞላው በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ ታላቅ ሰማዕትነትን የተቀበለው ሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስ አባቱ ቆዝሞስ (ስምዖን) እናቱ ኢየሉጣ ይባላሉ፡፡ ሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስ በሕዳር 15 ቀን የተወለደ ሲሆን ሀገሩ በታችኛው እስያ ልዩ ስሙ ሀንጌቤን ይባላል፡፡ ዘመኑ ዘመነ ሰማዕታት ነበርና መምለኬ ጣዖት የሆነው ንጉሥ እስክንድሮስ ቅድስት ኢየሉጣን ‹‹ለጣዖቴ ስገጂ›› ብሎ አስገደዳት፡፡ እርሷም ‹‹ሕጻኑ ልጄ መጥቶ ይመስክር›› ብላ ስትናገር ሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስ ተጠራና ተጠየቀ፡፡ ሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስም ‹‹ለጣዖት አንሰግድም፣ ዘላለማዊ የሆነ የማይሻር አምላክ ስላለ ለእርሱ ነው የምንሰግደው›› ብሎ የአምላኩን ክብር በሕፃን አንደበቱ መሰከረ፡፡ ሕፃኑም ይህንን በመሰከረ ጊዜ ዕድሜው ገና ሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ ነበር፡፡
እጅግ በጣም የሚገርመው ቅዱስ ቂርቆስ በከሃዲው ንጉሥ ፊት የጌታችንን ክብር በመሰከረ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ አርባ ጋን ውኃ የሚይዝ በርሜል አስጥዶ አርባ ቀን ሙሉ እሳት አስነድዶ ቅንጭብ፣ ዘይት፣ ዝፍጥና ሌላም በእጅጉ የሚጎዱ ነገሮችን በውስጡ ጨምሮ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ወደዚያ እቶኑ እሳት እንዲከቷቸው አዘዘ፡፡
ንጉሡ እስክንድሮስ ጭፍሮቹን “ሰም፣ ጨው፣ ባሩድ፣ሙጫ፣ እርሳስ፣ ብረትን፣ ቅንጭብ፣ ቁልቋል ጨምሩበት” ብሎ አዘዛቸው፡፡ ጭፍሮችም ያዘዛቸውን ከፈጸሙ በኀላ መጥተው “ያዘዝከንን ሁሉ ጨምረንበት ነዶ ፈልቷል” አሉት፡፡ “ድምፁም እንደ ነጎድጓድ ይሰማል፤ ወላፈኑም እንደ ፀሐይ ያንፀባርቃል፡፡ የፍላቱም ኃይል አሥራ አራት ክንድ ያህል እየዘለለ ይወጣል፡፡ በውስጡ የሚጣሉትን ሰዎች እዘዝ” አሉት፡፡ ያንጊዜም ህፃን ቂርቆስንና እናቱን ኢየሉጣን ይዘው ከእስር ቤት አወጧቸው፡፡ በክርስቶስ ስም ስላመኑ በእስር ቤት አግብተው አስረዋቸው ነበርና ፍላቱ ወደ ላይ በሚዘል በብረት ጋን ውስጥ ለመጨመር ሲወስዷቸው በዚያን ጊዜም እልፍ ከአንድ ሺህ አራት መቶ ሰዎች እንዲወጡና በፈላው የብረት ጋን ውስጥ የቅዱሳንን አሟሟት እንዲያዩ ሹሙ አዘዘ፡፡ ቅድስት ኢየሉጣም የፍላቱን ግርማ ባየች ጊዜ ተሸበረች፡፡ ተጠብቆላት ያለውንም ዋጋ ትታ ልትክድ ፈለገች፡፡ ቅዱስ ቂርቆስም ይህን ባወቀ ጊዜ “እናቴ ሆይ ከብረት ጋን ግርማ የተነሳ አትፍሪ፤ ድንጋፄም አይደርብሽ” እያለ ከብሉይና ከሐዲስ እየጠቀሰ እንድትጸና አስተማራት፡፡
“ነገር ግን እናቴ ሆይ አናንያንና አዛርያን፣ ሚሳኤልንም እግዚአብሔር ከዕቶን እሳት እንዳወጣቸው እወቂ፤ እኛንም ከዚህ ከብረት ጋን ውስጥ ሊያድነን ይችላል፡፡ እናት ሆይ ከሚያልፈው ከዚህ ዓለም ጭንቅ ልታመልጭ በሚያልፈው በዘለዓለም እሳት ልትቀጭ ትሻለች፡፡ እናት ሆይ ይህን አትሺ፤ ይቅርብሽ አሁን እግዚአብሔር በመካከላችን አለና ይረዳናል፡፡ ሶስናን ከሀጢያተኞች እጅ ያዳናት እኛንም ከብረት ጋን ያድነናል፡፡ ዳንኤልን ከአንበሶች አፍ ያዳነ እርሱ ያድነናል፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ብረት ጋን ውስጥ ግዳጃችን ልንፈፅም ፈቅዶም እንደሆነ የኢዮብን ነፃነት (ትእግስት) ልናገኝ ይገባናል፡፡ እርሱ ልጆቹንና ሚስቱን ያገኘው ገንዘብ ሁሉ አጥቶ በመጨረሻው ሰውነቱን አጥቶ ነበርና ምንም ምንም የቀረበለት አልነበረምና እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ ከማለት በቀር ያለው ነገር የለም እግዚአብሔር ሰጠ፤ እግዚአብሔርም ወሰደ አለ፡፡ የእግዚአብሔር ስሙ ለዘለዓለም ይመስገን አለ፡፡ እኛም ይህንን መከራ ልንታገስና የተጠበቀልንን ልንከተል ይገባናል…” እያለ አብዝቶ መከራት፡፡ ነገርግን በዚህም ምክር እናቱን መመለስና ለሰማዕትነት ማዘጋቸት አልቻለም፡፡ ከዚህ በኋላ ቂርቆስ ዓይኖቹን ወደሰማይ አቅንቶ መጸለይ ጀመረ፡፡ “እግዚአብሔር ሆይ ይህች ባርያህ ከምትክድ ከህይወት መፅሐፍ እኔን ፋቀኝ አለ፡፡ አቤቱ ይህነን ነገር ልታደርግ አይገባህም፤ አቤቱ እርሻውን ልታቃጥል ፍሬውንም ልትባርክ ትወዳለህን፡፡ አቤቱ እንጨቱን ቁረጡና አንድዱት ቅጠሉን ጠብቁ ብለህ ልታዝ አይገባህም፡፡ እንጨቱንም ቅጠሉንም ጠብቁ ብለህ እዘዝ እንጂ ይህ አይገባህም ያመነብህ ሁሉ ይህን ያየ ዘንድ፡፡ ማዳን የሚችል አምላክ ኑሮአቸው ቢሆን ከዚህ ከእሳት ባልሸሹም ነበር ብሎ እንዳይጠራጠር፡፡ ዲያብሎስ ከባለስልጣኑ ይልቅ እኔ በረታሁ ቅዱሳኑም ድል ነሳኋቸው ብሎ እንዳይመካ፣ ከመንጋውም አንድ በግ ቀማሁ እንዳይል አቤቱ የኃይል መንፈስ ለእናቴ ስጣት አበርታት…” ብሎ ጸለየ፡፡
በዚያን ጊዜ ዲያብሎስ ከእርሷ ሸሽቶ ሄደ፡፡ ከዚህ በኋላ ቅድስት እናቱ እንዲህ አለች፡- በመንግስተ ሰማያት አባት የሆንከኝ ልጄ ሆይ ጌታህ ኃይል ስጠኝ፡፡ የሚጠብቀንን ገድላችንን እንፈፅምና ድል እንነሣ” አለችው፡፡ የብረት ጋኑን ሲነድ ሳየው በምንጭ ላይ በዝቶ እንደሚወርድ ጠል ሁኖ አየዋለሁና፡፡ ቅዱሳንም ይህንን ሲነጋገሩ አንስተው ከብረት ጋኑ ውስጥ ጨመሯቸው፡፡ በውስጡም አንገትን የሚቆለምም ልብን የሚያጣምም ሆድን የሚሰነጥቅ ሥርንም የሚበጥስ መሣሪያ ነበረበት፡፡ ወዲያውም የራማው ልዑል ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥኖ ከሰማይ ወረደና የብረት ጋኑን እሳት ፈጽሞ አበረደው፡፡ ከቅዱሳንም አንዱን እንኳን ሳይነካው የብረት ጋን ማቃጠሉና መፍላቱ ፀጥ አለ፡፡ እንደ ውኃም ሆነ፡፡
ንጉሡም እሳቱ እንዳልጎዳቸው ሲያውቅ ከዚያ አውጥቶ በሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ አፍና አፍንጫ መርዝ ከተተበት፣ ነገር ግን መርዙ ምንም አልጎዳውም እንዳውም ምግብ ሆነው፡፡ ዳግመኛም ጨውና በርበሬ በዐይኑ አነደደበት፡፡ አሁንም ምንም አልነካውም፡፡ ከዚህም በኀላ ሹም እስክድሮስም አስራ አራት የተሳሉና የጋሉ ብረቶች ያመጡ ዘንድ ዳግመኛ አዘዘ፡፡ ሰባቱን በእናቱ አካል ሰባቱን በሱ አካል ውስጥ ይተክሉ ዘንድ ከነዚሁም ሁለቱን በጆሮዎቹ ሁለቱን በዓይኖቹ ሁለቱን በአፍንጫዎቹ አንዱን በልቡ ይተክሉ ዘንድ አዘዘ፡፡በሕፃኑም ላይ ሹሙ እንዳዘዘው አደረጉበት፡፡ አሁንም ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደና ፈወሳቸው፡፡
ዳግመኛም የሕጻኑን እራስ ከነቆዳው ገፈው በእሳት ውስጥ ይጨምሩ አንድ ሹም አዘዘ፡፡
እንዲሁም አደረጉበት፡፡ ዳግመኛም ቅዱስ ገብርኤል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥኖ መጥቶ ይህንን መከራ ከሕፃኑ አራቀለት፡፡ ዳግመኛም ሹሙ በመቃን ውስጥ ጨመረው በገመድ እንዲሰቅሉት አዘዘ፡፡ ከዚህም መከራ መልአኩ አዳነው፡፡ በዛሬዋ ዕለት ሐምሌ 19 ቀን በዓሉን በታላቅ ድምቀት የምናከብረው ይህንን ሁሉ የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤልን ተራዳኢነት በማሰብ ነው፡፡
ንጉሡም በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በብዙ ጭንቅና ሥቃይ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ለ3 ዓመታት አሠቃያቸው፡፡ እነርሱም መከራን እየተቀበሉ በከሀዲው ንጉሥ ፊት የአምላካቸውን ስም እየጠሩ መሰከሩ፡፡ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና ክብሩን ይመሰክሩለት ዘንድ የቢታንያን ድንጋዮችና የበለዓምን አህያ አንደበት ከፍቶ ያናገረ አምላክ ሦስት ዓመት እንኳን ባለሞላው በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወር ሕፃን ልጅ ላይ አድሮ በወቅቱ የነበሩ ዓላውያን ነገሥታት ክብሩን እንዲያውቁ አደረገ፡፡
በመጨረሻም ሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስ ተጋድሎውን ፈጽሞ ጥር 15 ቀን በ3 ዓመት ከ1 ወር ከ3 ቀኑ አንገቱን በሰይፍ ተቆርጦ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡ ሲሰየፍም ከአንገቱም ደም፣ ውኃና ወተት የወጣ ሲሆን ሦስት አክሊላትም ወርደውለታል፡፡ ጌታችንም የመከራውን ጽናት የትዕግስቱን ብዛት አይቶ ከመከራ ሊያሳርፈው ፈቀደና ተገልጾለት ‹‹ሰላም ለከ ኦ ፍቁርየ ቂርቆስ›› አለው፡፡ ‹‹ሰላም ላንተ ይሁን፤ የመከራህን ጽናት፣ የትዕግስትህን ብዛት አይቼ ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍህ መጣሁ›› ብሎ ብዙ ቃልኪዳን ሰጠው፡፡ ‹‹…ስምህ በተጠራበት፣ ቤተመቅደስህ በታነጸበት፣ ስዕልህ ባለበት ቦታ ሁሉ የሕፃናት እልቂት፣ የከብት በሽታ፣ የእህል እጦት ርሀብ፣ ቸነፈር አይደርስም›› የሚል አስደናቂ ቃልኪዳንም ገብቶለታል፡፡ ሕፃኑም በምድር ላይ አልተቀበረም ይልቁንም ጌታችን በኤልያስ ሰረገላ ሥጋውን አሳርጎለታል፡፡ እናቱ ቅድስት ኢየሉጣም በጥር 16 ቀን ሰማዕትቷን በክብር ፈጽማለች፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ እኛንም በአማላጅነታቸው የምታመን ሁላችንን
የብርሃናዊውን መልአክ የቅዱስ ገብርኤልን፣ የሕጻኑ ቂርቆስንና የቅድስት ኢየሉጣን ረድኤት በረከታቸውን ያሳድርብን፡፡ በጸሎታቸው ይማረን፡፡