Saturday, 21 November 2015

 “የኢየሱስ ክብሩ በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ነው”
እርግጥም እንዲሁ ነው ፡ በእውኑ ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሄር ነው ብላ በእግዚአብሄርነቱ ኢየሱስን የምታከብር ከኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን  የበለጠች ቤተክርስቲያን ማን ነች? ካቶሊክ ወይንስ ፕሮቴስታንት? ካቶሊክ አንዱን ጌታ ትከፍለዋለች ፡ ፕሮቴስታንት ደግሞ ሃያሉን አምላክ ታሳንሰዋለች ፤ እኛ ኦርቶዶክሳውያን ግን ያህዌውን ኢየሱስን እናመልካለን፡፡
ነገር ግን ይገርመኛል ፤ ለኦሪታውያን ጠላታቸውን እንዲጠሉ ፡ ወዳጆቻቸውን ደግሞ እንዲወዱ ተፃፈላቸው ፤ ለክርስቲያኖች ግን ወዳጆቻቸውን ብቻ ሳይሆን ጠላቶቻቸውንም እንዲወዱ ታዘዙ ፡ እንዲህም ነውና ኦርቶዶክሳውያን ይህን ሊፈፅሙ ይተጋሉ፡፡
ፕሮቴስታንቶችና ተረፈ ጴንጤ የሆኑ ተሃድሷውያን ግን ክርስቲያኖች ነን ይላሉ ወዳጆቻቸውን ግን ይጠላሉ ፡ ወዳጆቻቸውም የተባሉ ስለክርስቶስ መከራን የተቀበሉ ፡ አንዲቷን እምነት ያስተላለፉ ፡ በምልጃ የሚበረቱ ቅዱሳን ናቸው፡፡ ከቅዱሳንስ በላይ ለክርስቲያኖች ባልንጀራ ማን ሊሆን ነው? ፕሮቴስታንቶች ግን እኒህን የክርስቲያን ወዳጆች ጠልተዋል ፡ በዚህም አንድም ከክርስትና ርቀዋል ፡ ከኦሪታውያንም አንሰዋል (ኦሪት ወዳጅህን ውደድ ትላለችና)፡፡
መቼ ጠላን ይሉኝ ይሆናል ፡ ነገር ግን ስለነሱ በተወራ ጊዜ ሁሉ ከንቱ ቃል ያስቀድማሉ ፡ የንቀት ፌዝን ያሰማሉ ፡ ከክብራቸው ይልቅ ድካማቸውን በማጉላት ይጠመዳሉ ፡ ነገር ግን ክርስቶስ ያፀደቃቸውን ማን ይከሳቸዋል? እኒህ ግን እግዚአብሄር ያከበራቸው እንደዲያቢሎስ ሊከሱ ይሞክራሉ፡፡
ስለቅዱሳን ባላቸውም ጥላቻ ስለኢየሱስ አብዝተው ሲያወሩ እናያቸዋለን ፡ የኢየሱስን ስም መጥራት ህይወት ይመስላቸዋልና ይስታሉ ፡ “ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ” የሚሉ ጌታ ኢየሱስን ግን ያላወቁ እኒህ ናቸው ፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር ሲሆን ፍቅርን ግን አጥተው ይመላለሳሉና ፡ ስለፍቅራቸው ማነስም በክርስቶስ ከተመሰረተች ክርስትና ርቀው ከኦሪታውያንም አንሰው ይታያሉ፡፡
ስለሆነም ስለቅዱሳን በጎ መናገርን አይወዱም ፡ አንድም ስለቅዱሳን የሚናገር ሰው ሲመለከቱ ይቆጣሉ ፡ ራሳቸውን ቅዱሳን ስለማለት ግን አያፍሩም ፡ የቅዱሳንን አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስንም ይጠራሉ ፡ ክርስቶስ ያከበራቸውን ደግሞ ይንቃሉ ፡ አለማውያን ማለት እኒህ ናቸው፡፡ ራሳቸውን ለማፅደቅ አንደኞች ቅዱሳንንም ለማሳነስ ፈጣኖች አለማውያን ማለት እኒህ ናቸው፡፡ ከፍቅር የተለዩ ፍቅር ክርስቶስን ግን የሚጠሩ እኒህ ናቸው፡፡ ኢየሱስ ኢየሱስ የሚልይ ኢየሱስን ግን ከአብ አሳንሰው በሁለት የሚበላለጡ አማልክት የሚያመልኩ እኒህ ናቸው፡፡
ከእነዚህ አለማውያን ተለዩ ፡ ከእነዚህ ፍቅር የራቃቸው ተለዩ ፡ ከእነዚህ አላዋቂወች ተለዩ ፡ የኢየሱስ ክብሩ በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ነውና ፡ ኢየሱስን የምትወዱ ክብሩን ከሚይሰፉ ጋር ተባበሩ፡፡

Thursday, 12 November 2015

የተሐድሶ መረብ

የተሐድሶ መረብ አድማስና የትኩረት አቅጣጫዎች

ኅዳር 2 ቀን 2008 ዓ.ም
ክፍል ሦስት
ባለፉት ሁለት ተከታታይ ጽሑፎች ተሐድሶ መናፍቃን በምን ዐይነት መንገድ ምእመናንን እየነጠቁ እንደሆነ ተመልክተናል፡፡ ከዚህ ቀጥለን በምናወጣቸው ተከታታይ ጽሑፎች ደግሞ የተሐድሶ አድማሱ የት ድረስ እንደሆነ ለአንባቢያን ግንዛቤ የሚሰጥ መረጃ የምናቀርብ ይሆናል፡፡

የተሐድሶ እንቅስቃሴ ዓለም አቀፋዊ መልክ ያለውና በዓለም ላይ ባሉ የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ላይ በፕሮቴስታንት የእምነት ተቋማት የተቃጣ ስውር ሴራ ነው፡፡ እንቅስቃሴው ከውጪ ወደ አገር ውስጥ የመጣ ስለሆነ የተሐድሶው አቀንቃኞች በአሳብ፣ በገንዘብ፣ በቁሳቁስ፣ ወዘተ ከሚያግዟቸው በልማት ስም ከተቋቋሙ ድርጅቶች ጋር ከፍተኛ ቁርኝት አላቸው፡፡ ከእነዚህ ድርጅቶች እና ከፕሮቴስታንት ቸርቾች በሚበጀት በጀት፣ ከአገር ውስጥ እስከ ውጪ አገር በተዘረጋ መዋቅር፣ ቤተ ክርስቲያንን ከተቻለ ሙሉ በሙሉ ለመረከብ ፕሮቴስታንት ለማድረግ ካልሆነም ለሁለት ለመክፈል በሚያስችል ስልት እየሠሩ እንደሆነም ተመልክተናል፡፡

በአገር ውስጥ ያሉት ሠላሳ የሚደርሱ የተሐድሶ ማኅበራት የቤተ ክርስቲያን ምንጮች በሆኑት የአብነት ትምህርት ቤቶች፣ ገዳማት፣ መንፈሳዊ ኮሌጆች፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት ላይ እንዲሁም መዋቅራዊ ድጋፍ ለማግኘት የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅር ላይ ይሠራሉ፡፡ የተለያዩ መመዘኛዎችን በመጠቀም ትኩረት አድርገው የሚሠሩባቸው ቦታዎች አሉ፡፡ መነሻቸውን አዲስ አበባ ላይ አድርገው በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች ሰፋ ያለ እንቅስቃሴ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ ከዚህ ዕትም ጀምሮ በተከታታይ ጽሑፎች ከመነሻቸው ከአዲስ አበባ ጀምረን ትኩረት ሰጥተው በሚሠሩባቸው አካባቢዎች ያለውን እንቅስቃሴ እንመለከታለን፡፡

አዲስ አበባን ማእከል ያደረገው የተሐድሶ መረብ
አዲስ አበባ የተሐድሶ እንቅስቃሴው ማእከል ነው፡፡ ታሪክ የሚነግረን ተሐድሶዎች እንቅስቀሴው ሲጀመር ጀምሮ ማእከላቸውን አዲስ አበባ አድርገው ወደ ሌሎቹ የአገራችን ክፍሎች ኑፋቄያቸውን ያስፋፉት መሆኑን ነው፡፡ አዲስ አበባ ተሐድሶዎች በየአጥቢያው ተወካዮችን አስገብተው ብዙ ሥራ የሚሠሩበት፣ የተለያዩ የሥልጠና መስጫ ተቋማትን እና ኮሌጆችን ያቋቋሙበት፣ የቤት ለቤት ሥራዎችን በሰፊው የሚሠሩበት፣ የጽዋ ማኅበራትን በብዛት የፈጠሩበት፣ ከክፍለ ሀገር ለሚያመጧቸው ካህናትና ዲያቆናት ሥልጠና የሚሰጡበት ነው፡፡ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር የሚያስተላልፉት፣ አብዛኛው የተሐድሶ መናፍቃን መጻሕፍት የሚታተሙት፣ የገንዘብ ልገሳ የሚያደርጉላ ቸው የመናፍቃን ድርጅቶች የሚገኙት አዲስ አበባ ነው፡፡ ፕሮቴስታንታዊ የአምልኮ ሥርዓት የሚፈጸምባቸው የተሐድሶ አዳራሾች በስፋት የሚገኙትም እዚሁ ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያንን ለማፍረስ የሚያስችላቸውን መዋቅራቸውን የዘረጉትና ስልታቸውን የነደፉት አዲስ አበባን ማእከል አደርገው ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት ከአዲስ አበባ እየተነሡ ያልደረሱበት የአገራችን ክፍል የለም ማለት ይቻላል፡፡ አዲስ አበባ ላይ ያላቸው መረብም ጠንካራና ሁሉንም አጥቢያዎች የሚያቅፍ ለማድረግ እንቅልፍ አጥተው በመሥራት ላይ ናቸው፡፡ መሐል አዲስ አበባ አካባቢ ካሉት አጥቢያዎች ተነቅቶባቸው ሲባረሩ በአዲስ አበባ ዙሪያ ወደሚገኙ አጥቢያዎች በመሔድ ተመሳስለው ገብተው የቅሰጣ ሥራቸውን ይሠራሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያን ተልእኳቸውን ተረድታ በውግዘት የለየቻቸውና አጋልጣ ምእመናን እንዲያውቋቸው ያደረገቻቸው ተሐድሶዎች ከጀርባ ሆነው በየአጥቢያው የሰገሰጓቸው ተሐድሶ መናፍቃን ተልእኳቸውን ያፋጥኑላቸዋል፡፡

እንቅስቃሴው በግልም በቡድንም እንዲሁም በድርጅት ስም የሚካሔድ ነው፡፡ በግለሰብ ደረጃ የተሐድሶ አቀንቃኞችን እገሌ ወእገሌ ማለቱ ባያቅትም ለአንባቢም ሆነ ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጠው ጥቅም ካለመኖሩና እነርሱንም የበለጠ እንዲደበቁ ዕድል መስጠት ስለሚሆን ይህንን መጠበቅ የለብንም፡፡ ነገር ግን በብዙ ቦታዎች እንደሚታየው በዓላማ እንቅስቃሴውን የሚመራው አካል አንድ ወይም ጥቂት ነው፡፡ ሌላው ግን ምን እየተሠራ እንደሆነ እንኳን ሳያውቅ ሌሎቹ ስለሔዱ ብቻ የሚከተል ነው፡፡

በተደጋጋሚ ከተለያዩ የአገራችን ክፍሎች ካህናትን እያመጡ አዲስ አበባ ላይ ያሠለጥናሉ፡፡ በተለይ ከገጠር ለሥልጠና የሚያመጧቸው ካህናት ከጥቂቶቹ በስተቀር በየዋህነት ጉዳዩ ምን እንደሆነ ሳይረዱ የሚመጡ ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ ቤተ ክርስቲያንን የማፍረስ ሴራዎች ያውም የቤተ ክርስቲያን ምንጮች ያልናቸው አብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማት ላይ ሓላፊነት ላላቸው ሰዎች ተሰጥቶ የፈለጉት ነገር አለመሳካቱን ስናይ የእግዚአብሔርን ጠብቆት እናደንቃለን፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ለማፍረስ የሚሰጡት ሥልጠና ውጤት ማምጣት ያልቻለው በአንድ በኩል ከሠልጣኞች አቅም ማነስ የተነሣ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ የሚከተሉት ዓላማ የጥፋት በመሆኑ እግዚአብሔር እንዳይሳካላቸው ቤተ ክርስቲያንንና ምእመናንን በረድኤት ስለሚጠብቃቸው ነው ብለን እናምናለን፡፡ ተሐድሶዎችም ምዕራባውያን ቤተ ክርስቲያንን የማፍረስ ስውር ተልእኳቸውን ለማሳካት የበጀቱት ዳጎስ ያለ ገንዘብ እንዳይቀርባቸው እንጂ ለጽድቅ ስለ ማይሠሩ ለሪፖርት ብቻ ሥልጠና ሰጥተው የሚልኳቸው ብዙዎችን ነው፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መቦርቦርን እንጀራ ማብሰያ አድርገው የያዙት ብዙ የተሐድሶ ድርጅት አንቀሳቃሾች መናሃሪያቸው አዲስ አበባ ነው፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባዔ የተወገዙና ከሥልጣነ ክህነታቸው የተሻሩ ግለሰቦች ሳይቀሩ የክህነት ስማቸውን ተጠቅመው ዲያቆን፣ መሪ ጌታ እያሉ መጻሕፍት ያሳትማሉ፡፡ ሥልጠና የሚሰጡባቸው፣ ኑፋቄያቸውን የሚዘሩባቸው፣ በእነርሱ አነጋገር አምልኮት የሚፈጽሙባቸው፣ በሥውር ቤተ ክርስቲያንን የማፍረስ ሴራ የሚጠነስሱባቸው፣ የቴቪዥን መርሐ ግብራትን የሚቀርጹባቸው፣ የግልና የኪራይ አዳራሾች አሏቸው፡፡ በእነዚህ አዳራሾች ሲያሻቸው ያስጨፍራሉ፣ ሲያሻቸው እንፈውሳለን ይላሉ፣ ሲያሻቸው ደግሞ እነርሱ ሳይማሩና የያዙት ወንጌል ሳይገባቸው ያስተምራሉ፡፡

የቤት ለቤት ቅሰጣ አልበቃ ብሏቸው በመገናኛ ብዙኀን ወደ ሕዝብ መድረስ ጀምረዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ምእመናን ስለ ተሐድሶ ያላቸው ግንዛቤ እየጨመረ መምጣቱ፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ከተሐድሶዎች ጋር እያደረጉት ያለው ትንቅንቅ መጎልበቱና ለምእመናን የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብራት እየበረከቱ መምጣታቸው ይበል የሚያሰኝ ቢሆንም፤ አዲስ አበባን ሙሉ በሙሉ ከተሐድሶዎች እጅ ነፃ ለማድረግ ግን ሰፋ ያለና የተቀናጀ ሥራ የሚጠይቅ ነው፡፡

አጥቢያቸው የሚገኘውን ሰንበት ትምህርት ቤት አፍርሰው ሌላ ሰንበት ትምህርት ቤት ለማቋቋም፣ አባላቱን ለሁለት ከፍለው አገልግሎቱ እንዳይካሔድ ለማድረግ የሚጥሩ ከተሐድሶ በሚገኝ ገንዘብ የሚደለሉ አንዳንድ አስተዳዳሪዎችና የስብከተ ወንጌል ሓላፊዎች መኖራቸው የሚታወቅ ነው፡፡ ዓላማችንን ያስፈጽሙልናል ያሏቸውን የሰንበት ተማሪዎች ሰብስበው የተለየ ትምህርት ካስተማሩ በኋላ ተልእኮ ሰጥተው ተመልሰው ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ እንዲገቡ የሚያደርጉ፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ሌላ ተልእኮ ይዘው ተመሳስለው የገቡትን የጥፋት መልእክተኞች አካሔድ አጢነው ሲያግዷቸው ለምን ታገዱ ብለው ሰንበት ትምህርት ቤቱን ለመዝጋት የሚነሡ የስብከተ ወንጌል ሓላፊዎች እየበዙ መጥተዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው ምን ያህል ተመሳስለው ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንደገቡ ነው፡፡ ምእመናንም ሆኑ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች እንዲህ ዓይነት የጥፋት ተልእኮ አንግበው የሚንቀሳቀሱትን ወገኖች ሲመለከቱ ማንነታቸውን የሚያሳይ መረጃ መሰብሰብ፣ ከማን ጋር እንደሚውሉ፣ ምን እንደሚሠሩ፣ አነጋገራቸው፣ አካሔዳቸው፣ ኦርቶዶክሳዊነታቸው ምን እንደሚመስል ማጣራት ይኖርባቸዋል፡፡

በአንዳንድ አጥቢያዎች ገድላትና ድርሳናት፣ ተአምረ ማርያምና ስንክሳር እንዳይነበቡ የሚከለክሉ አስተዳዳሪዎች አሉ፡፡ የጠበል ቦታ አያስፈልግም ብለው ለጋራዥ በማከራየት ገንዘብ ከመመዝበር አልፈው ምእመናንን ከድኅነት የሚለዩና የተሐድሶ አጋርነታቸውን የሚገልጡ ወገኖች አሉ፡፡ ተሐድሶዎቹ ከእንደዚህ ያሉ የጫኑዋቸውን ተሸክመው ለማስፈጸም ከሚደክሙ አካላት ጋር በመመሳጠር ዐውደ ምሕረትን ለመቆጣጠር ጥረት እያደረጉ ነው፡፡ ነገር ግን በሰንበት ት/ቤት ወጣቶችና በጠንካራ ምእመናን ተጋድሎ ዓላማቸው አልተሳካም፡፡ ሰባክያነ ወንጌልን የሚመድቡትና የማስተማር ሓላፊነት የተሰጣቸው አንዳንድ የስብከተ ወንጌል ሓላፊዎች በዐውደ ምሕረት ላይ ወጥተው ሲያስተምሩ ስለ ቅዱሳን ማስተማር የኢየሱስን ማዳን ይሸፍናል ሲሉ ይሰማሉ፡፡ የሚጋብዟቸው መምህራን ደግሞ ኢየሱስን ብቻ እንሰብካለን የሚል መፈክር አንግበው ይንቀሳቀሳሉ፡፡ እነዚህ ወገኖች ያልገባቸው ወይም አውቀው ለማደናገር የሚጥሩት ስለ ቅዱሳን መስበክ ስለኢየሱስ ክርስቶስ መስበክ መሆኑን ነው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ በአንዳንድ አጥቢያዎች አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናት ተጀምረው ሳይጠናቀቁ ገና በመቃኞ እያሉ እና አጸዱ እንኳን ቅጥር ሳይኖረው ሁሉም ቁሳቁስ የተሟላለት ዘመናዊ አዳራሽ የሚሠሩም አሉ፡፡ ለምን ተብለው ሲጠየቁ ለወንጌል ቅድሚያ መስጠት ተገቢ ስለሆነ የሚል መልስ ያቀርባሉ፡፡ በእውነቱ የሰው ልጅ ድኅነት ማግኘት ገድዷቸው ይህን ቢያደርጉ መልካም ነበር፡፡ የእነሱ ዓላማ ግን ሌላ ነው፡፡ ሰዎች ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ እንዲቀሩ ማድረግ፡፡ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን አሳንሶ አዳራሾችን ዘመናዊ አድርጐ መገንባት የተሐድሶዎች አንድ ስልት ተደርጎ እየተሠራበት ነው፡፡ ይህንን አካሔድ የሚቃወሙትንየወንጌል ጸሮች እያሉ ይሳደባሉ፤ ምእመናን እንዲጠሏቸው ያደርጋሉ፡፡ ለአካሔዳቸው እንቅፋት ይሆናሉ ያሉዋቸውን በሓላፊነት የሚገኙ አገልጋዮች ማባረር፣ ያላጠፉትን ይህን ጥፋት ፈጸሙ በማለት የሀሰት ስም መስጠት፣ ማብልጠልና ከምእመናን ጋር ማጋጨት በአዲስ አበባ የተለመደ እየሆነ መጥቷል፡፡ በዚህ ምክንያትም በየፖሊስ ጣቢያውና በየፍርድ ቤቱ ሲጓተቱ የሚውሉ አገልጋዮች ቁጥር ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ መጥቷል፡፡

ይህ አካሔድ በቶሎ መፍትሔ ካልተሰጠው ከቅዳሴ በኋላ ዐውደ ምሕረት ላይ ተአምረ ማርያም ሳይነበብ ምእመናን ወደ አዳራሽ እንዲገቡ መደረጉ የማይቀር ነው፡፡ እነዚህ እና የመሳሰሉት አስተዳደራዊ ጉዳዮች ሽፋን ተደርገው የሚሠሩ የተሐድሶ ቅሰጣዎች ናቸው፡፡

ሌላው ደግሞ በግልጽ የሚሠራው የተሐድሶ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ለምሳሌ፡- ፍል ውኃ አካባቢ የሚገኝ ተስፋ ተሐድሶ የሚባል ድርጅት አለ፡፡ ይህ ድርጅት ላለፉት ሦስትና ዐራት ዓመታት ከተለያዩ ቦታዎች ለተውጣጡ የገዳማት አበምኔቶች፣ የአብነት ትምህርት ቤት መምህራን፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለሚያገለግሉ ቀሳውስትና ዲያቆናት ሥልጠና እየሰጠ በሰርተፊኬት አስመርቋል፡፡ ከ፳፻ወ፮ ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ ፍኖተ ሕይወት ማኅበረ መድኀኔዓለም የተስፋ ተሐድሶ መጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቤት የሚባል ተቋም ከፍቶ በዲፕሎማ ማስመረቅ ጀምሯል፡፡ ድርጅቱ ነሐሴ ፲፰ ቀን ፳፻ወ፮ ዓ.ም ደግሞ Integrated Theological Training and Skill Development for Africa ከሚባል ኮሌጅ ጋር በመተባበር የመጀመሪያ ዙር ዐሥር ተማሪዎችን በዲፕሎማ አስመርቋል፡፡

በአጠቃላይ የአዲስ አበባ እና ዙሪያውን እንቅስቃሴ ስንመለከት በገንዘብ ጥማት ልቡናቸው በታወረ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች፣ በተሐድሶ እንቅስቀሴ መረብ ውስጥ ባሉ ስብከተ ወንጌል ሓላፊዎች እና በፕሮቴስታንት ድርጅቶች ጥምረት የሚካሔድ ነው፡፡ ገንዘብ እስካገኙ ድረስ ለቤተ ክርስቲያን ዶግማና ቀኖና ደንታ የሌላቸው የቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች ባሉባቸው አጥቢያዎች እና ከተሐድሶዎች ጋር ከፍተኛ ቁርኝት ያላቸው የስብከተ ወንጌል ሓላፊዎች ባሉባቸው አጥቢያዎች ዐውደ ምሕረቱ የሚፈቀደው ለኦርቶዶክሳውያን ሳይሆን ለተሐድሶ መናፍቃን ነው፡፡ በአዲስ አበባ ዙሪያ ያለው እንቅስቃሴ በዚህ መልክ የሚቀጥል ከሆነ ከጊዜ በኋላ የተወሰኑ አጥቢያዎች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አይደለንም ማለታቸው የማይቀር ነው፡፡
ሰሜኑን ማእከል ያደረገ የተሐድሶ እንቅስቃሴ
ይህ እንቅስቃሴ የክርስትና መሠረት የተጣለበትን ሰሜኑን የአገራችንን ክፍል ለማጥፋት ታቅዶ የሚካሔድ ነው፡፡ እንቅስቃሴው ጥንታውያን ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በትምህርት ስም፣ በማኅበራዊ ልማቶች ስም፣ በእርቅና ሰላም ስም፣ ማረሚያ ቤቶችን እናግዛለን በሚል ስም ምእመናን እና ሕፃናት ላይ ትኩረት አድርገው ይሠራሉ፡፡ የዚህ እንቅስቃሴ ፊታውራሪዎች ከሣቴ ብርሃን የተሐድሶ ድርጅት፣ መሠረተ ክርስቶስ ቸርችና የኢትዮጵያ አዲስ ኪዳን መጥምቃዊት ቸርች ሲሆኑ በግለሰብ ደረጃ እንቅስቃሴው ውስጥ ታላቅ ሱታፌ ያላቸው ግለሰቦች አሉ፡፡

ከሣቴ ብርሃን ከመወገዙ በፊትም የትኩረት አቅጣጫው የነበረው ሰሜኑ የአገራችን ክፍል ነበር፡፡ የከሣቴ ብርሃን ቅጥረኞቹ ጽጌ ሥጦታው፣ ሠረቀ ብርሃን ዘወንጌል፣ ጌታቸው ምትኩ፣ ባዩ ታደሰና ሙሴ መንበሩ ከአዲስ አበባ ተነሥተው በጎጃም በር ወጥተው ሥልጠና ሰጥተው፣ ቅኝት አድርገውና አዳዲስ ተከታዮች አፍርተው በሸዋ በር ይመለሳሉ፡፡ በ፳፻ወ፯ ዓ.ም ብቻ ሸኖ፣ አንጾኪያ፣ ደሴ፣ ጎንደር፣ ባሕር ዳር ሁለት ጊዜ እና አዲስ አበባ ላይ ከተለያዩ አብያተ ክርስቲያናትና አብነት ትምህርት ቤቶች ለተውጣጡ በአጠቃላይ ከሁለት መቶ በላይ ለሚሆኑ ካህናትና የአብነት መምህራን ሥልጠና ሰጥተዋል፡፡ ሥልጠናውን የሚወስዱት ሰዎች የሚመለመሉት በከሣቴ ብርሃን ቢሆንም ሥልጠናው የሚሰጠው በፕሮቴስታንት አዳራሾችና በፕሮቴስታንት ፓስተሮችም ነው፡፡

ከ፳፻ወ፭ ዓ.ም ጀምሮ ብሔራዊ ተሐድሶን አመጣለሁ እያለ ሌሎችን የተሐድሶ ድርጅቶች ሲቀሰቅስና ሲያስተባብር የነበረው ይኸው ድርጅት ባለፈው ዓመት የወንጌል አገልግሎት ማኅበራት ኅብረት የሚባለው እናት የተሐድሶ ድርጅት እንዲቋቋም አስተዋጽኦው ከፍተኛ ነው፡፡ ስሙን በመጀመሪያው የኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ስም ሠይሞ ስለሚንቀሳቀስ የቤተ ክርስቲያን አካል መስሎ የሚታያቸው ብዙዎች ናቸው፡፡ ያለ ቤተ ክርስቲያን ዕውቅናና ፈቃድ ከተከፈቱት የቴሌቪዥን መርሐ ግብሮች በተጨማሪ ፳፻ወ፬ ዓ.ም ላይ የተወገዘው ከሣቴ ብርሃን የተሐድሶ ድርጅትም መጥቅዕ የተባለ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር ሊጀምር ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡

ሁለተኛው የሰሜኑ የአገራችን ክፍል የተሐድሶ እንቅስቃሴ ፊታውራሪ የሆነችው መሠረተ ክርስቶስ ቸርች ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ሰሜኑን በወንጌል እንወርሳለን የሚል ፕሮጀክት ነድፋ እየሠራች ሲሆን ፕሮጀክቱ በየዓመቱ በሚሊዮን የሚቆጠር ብር ፈሰስ እየተደረገ የሚሠራ ነው፡፡ መሠረተ ክርስቶስ እንደሽፋን ተጠቅማ ሰሜኑ ላይ ትኩረት አድርጋ የምትሠራው ሁለት ፕሮጀክቶችን ነው፡፡ እነዚህ ፕሮጀክቶች ሰሜኑን በወንጌልና የማረሚያ ቤቶች አገልግሎት የሚባሉ ናቸው፡፡ የእነዚህ ፕሮጀክቶች ዋና የትኩረት አቅጣጫ ሰሜኑ የአገራችን ክፍል ቢሆንም በሌሎች አካባቢዎችም ተመሳሳይ እንቅስቀሴዎችን ታደርጋለች፡፡

ሰሜኑን በወንጌል የሚባለው ፕሮጀክት በትግራይ፣ ጎንደር፣ ወሎ፣ ጎጃምና ሸዋ አካባቢ በከፍተኛ ሁኔታ እንቅስቃሴ እያደረገች ነው፡፡ በእነዚህ አካባቢዎች የተለያዩ አጥቢዎች፣ የአብነት ትምህርት ቤቶችና ማረሚያ ቤቶች ላይ ትኩረት አድርጋ እየሠራች ነው፡፡ ለዚህ ዓላማ ማስፈጸሚያ የሚሆን ገንዘብ የምታገኘው ከተለያዩ የውጪ ድርጅቶች (የፕሮቴስታንት) ከሚላክ ገንዘብ፣ በሚያውቋቸው ሰዎች ከውጪ ከሚሰበሰብ እርዳታ እና ያሠለጠኗቸውን ሰዎች በቪሲዲ በመቅረፅና እርሱን በማሳየት ከደጋፊ ዎች በሚገኝ ገንዘብ ነው፡፡ የመሠረተ ክርስቶስ የልማት ድርጅት (Meserete Kirstos Church Relief Development) የታላቁ ተልእኮ አገልግሎት አጋር ስለሆነ ከዚህ ድርጅትም የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ ይደረግላታል፡፡

የዚህ እንቅስቃሴ ዓላማ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ካህናት፣ ዲያቆናትና መሪጌቶች በገንዘብ በማታለል፣ የተለያዩ ሥልጠናዎችን በማዘጋጀት፣ ማንነታቸውን መለወጣቸው እንኳን ሳይታወቃቸው የተሐድሶ እንቅስቃሴው አጋርና ቀኝ እጅ እንዲሆኑ በማድረግ በውስጥ ሆነው የተሐድሶ ሥራ እንዲሠሩ ተልእኮ መስጠት ነው፡፡ ሥልጠና የሚሰጡላቸው ደግሞ የተሐድሶውን እንቅስቃሴ ዓላማ ብለው የያዙት እነ ሠረቀ ብርሃን ዘወንጌል፣ ጽጌ ሥጦታው፣ አግዛቸው ተፈራ፣ የዕድል ፈንታ፣ ታምራት፣ ፓ/ር ሰሎሞን ከበደ፣ ወዘተ ናቸው፡፡

በ፳፻፮ ዓ.ም ብቻ ከተለያዩ የአገራችን ክፍሎች ለመጡ ከሃምሳ በላይ ለሚሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወረዳ ቤተ ክህነት፣ ሊቃነ ካህናት፣ የቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት ሥልጠና ሰጥታለች፡፡ ሥልጠናው በተለያዩ ዙሮች መሐል ሜዳ፣ አዲስ አበባና ደብረ ዘይት ላይ የተካሔደ ነበር፡፡ ስለ እርቅና ሰላም አስተምራለሁ በሚል ሰበብ የማሠልጠኛ ሰነድ አዘጋጅታ የራሷን ዶክትሪን እያስተማረች ነው፡፡ ለዚሁ ዓላማ በ፳፻ወ፯ ዓ.ም የብርሃን ፍሬ የሚባል የበጎ አድራጎት ድርጅት አቋቁማለች፡፡ የበጎ አድራጎቱ መመሥረት ዋና ዓላማ በልማት ስም ምንፍቅናን ማስፋፋት ሲሆን “ወንጌልን ማስፋፋት ዋና ዓላማችን ቢሆንም በውስጠ ታዋቂነት የሚሠራ እንጂ ከመተዳደሪያ ደንቡ ላይ አይቀመጥም” በማለት በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ የተቀመጡት የበጎ አድራጎት ማኅበሩ “የማስመሰያ” ዓላማዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡

1.የቂም በቀል፣ ደም የመመለስ ወይም የጥቁር ደም፣ የነፍስ ግድያ ባህልና ግጭትን እንደ ጀግንነት የመቁጠር ልማድን ለኅብረተሰቡ በማስተማር ማስወገድ፣

2.ኋላ ቀር የሥራ ባህልን፣ ከአቅም በላይ መደገስንና አባካኝነትን፣ ያለ ዕድሜ ጋብቻን፣ የትዳር መፍረስንና የቤተሰብ መበተንን፣ ለዕድገትና ለሰላም ጠንቅ የሆኑ አስተሳሰብ አመለካከትና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ኅብረተሰቡን በማስተማርና በማማከር ማስወገድ፣

3.በልዩ ልዩ ሱሶችና መጥፎ ልማዶች ተጠምደው ጎጂ ልማደኛ ሆነው ጎዳና ውስጥ ያሉ ወጣቶችን ካሉበት ሱስና መጥፎ ልማድ እንዲወጡ መርዳት፣

4.የአቅም ግንባታ የመልካም ሥራ ሠርቶ ማሳያ ልማቶችን መሥራት ናቸው፡፡

በማረሚያ ቤቶች ውስጥ በእርዳታ ሰበብ በመግባት በሃምሳ ስድስት (፶፮) ማረሚያ ቤቶች ላይ የእምነት ማስፋፋት ሥራ እየሠራች ሲሆን ታራሚዎቹ ሲወጡ በሚሔዱበት ቦታ የራሳቸው “ቸርች” እንዲያቋቁሙ ተልእኮ ትሰጣለች፡፡ በሃያ አንዱ (፳፩) ማረሚያ ቤቶች ደግሞ መደበኛ ሠራተኞች ተቀጥረው ይሠራሉ፡፡ አብዛኛዎቹ ተቀጣሪዎች በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዲቁናና በሰንበት ትምህርት ቤት ሲያገለግሉ የነበሩ ተሐድሶዎች ናቸው፡፡ ስውሩ የእምነት ማስፋፋት ሥራቸው እንዳይጋለጥ የተወሰኑ ማረሚያ ቤቶች ላይ የልማት ሥራዎችን ይሠራሉ፡፡ የተወሰኑ ማረሚያ ቤቶች ላይ ቤተ መጻሕፍትና ካፍቴሪያ ሠርተው ሰጥተዋል፡፡ ለታራሚዎች የልብስና የሳሙና እርዳታ ያደርጋሉ፡፡

መሠረተ ክርስቶስ ከእነዚህ ሁለት ዋና ዋና ፕሮጀክቶች በተጨማሪ በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች በትምህርትና አቅም ግንባታ፣ በምግብ ዋስትና፣ በልማት፣ የተፈጥሮ አደጋን እና ኤች አይ ቪ ኤድስን በመከላከል ስም በመግባት ምእመናንን የመቀሰጥ ሥራ ትሠራለች፡፡ አዲስ አበባ፣ ናዝሬት፣ ደብረ ዘይት፣ ሆለታ፣ ማርቆስ፣ ሜታ ሮቢ፣ መሐል ሜዳ፣ ጀልዱ፣ ቀዋ ገርባ፣ ወዘተ እነዚህ ፕሮጀክቶች ተፈጻሚ የሆኑባቸውና ውጤት ያመጡባቸው ቦታዎች ናቸው፡፡ የልማት ሥራዎች መሠራታቸውን ማንም ኢትዮጵያዊ አይቃወምም፣ ነገር ግን በልማት ስም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምእመናንን በመንጠቅ፣ ከማንነቱ መለየትና ከርስት መንግሥተ ሰማያት በኣፍአ እንዲቀር ማድረግ ተገቢ እንዳልሆነ ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ እኛ የምንቃወመውም ርዳታውን እና ልማቱን ሳይሆን ከልማቱ በስተጀርባ ያለውንና ሰውን ከሃይማኖት መለየቱን ነው፡፡

የኢትዮጵያ አዲስ ኪዳን መጥምቃዊት ችርች ደግሞ በትምህርት ዘርፍ ላይ ተሰማርታ ሕፃናት ላይ ትኩረት አድርጋ የምትሠራ ናት፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች ትምህርት ቤት በመክፈት በቅናሽ ዋጋ እና ለወላጆች በሚደረግ ድጋፍ ስም የራሷን የእምነት ማስፋፋት ሥራ እየሠራች ነው፡፡ እስካሁን የእንቅስቃሴው አድማስ በሰሜን ሸዋ ዞን ዓለም ከተማ ወረዳ ላይ ቢሆንም ከተነደፈው ፕሮጀክትና ይዘውት ከተነሡት ግብ አንጻር በዚህ እንደማያቆም ግልጽ ነው፡

ሌላው መነሣት ያለበት ጉዳይ ባለፉት ቅርብ ዓመታት ትግራይ አካባቢ እየተካሔደ ያለው የተሐድሶ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ማኅበረ ሰላማ መወገዙ የሚፈልገውን የቅሰጣ ተግባር ከመሥራት አልከለከለውም፡፡ እንዲያውም አድማሱን አስፍቶ ከምእመናን ወጥቶ በየዩኒቨርሲቲው የሚማሩ ተማሪዎችን እና የቅዱስ ፍሬምናጦስ ከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትን በመሰብሰብ በሥውር ማሠልጠንና ማስተማር ጀምሯል፡፡ ከማኅበረ ሰላማ በተጨማሪ ባለፈው ዓመት ትግራይ ተሐድሶ መንፈሳዊ ማኅበር (ቤተ ክርስቲያን) የሚባል የተሐድሶ ማኅበር ተመሥርቷል፡፡ ይህ ማኅበር ደንብ ቀርጾ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ለማፍረስ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ ይህ ሁሉ የሚያሳየን እየተካሔደ ያለው የተሐድሶ እንቅስቃሴ አድማሱ ምን ያህል ሰፊ እንደ ሆነና አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ሰሜኑን የአገራችንን ክፍል ምን ያህል ትኩረት እንዳደረጉበት ነው፡፡

የአንድ አገር ልማትና ዕድገት ወደ ላቀ ደረጃ የሚደርሰው የሃይማኖት፣ የዘር፣ የቀለም ገደብ ሳይገድበው በተባበረ ክንድ ሲሠራ መሆኑ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ ጤነኛ አእምሮ ያለው ሰው ሁሉ የአገሩን ልማትና የኅብረተሰቡን ዕድገት የሚጠላ አይሆንም፡፡ ሆኖም የልማቱ ተባባሪዎች ነን የሚሉ አካላት ፊት ለፊት ሰውን የሚያሳሱና መልካም የሚመስሉ ነገሮችን እያሳዩ ውስጣቸው ግን በማር የተለወሱ መርዞች ይዘውና ሌላ ተልእኮ አንግበው የሚንቀሳቀሱ ከሆነ ልማቱም ልማት፣ ዕድገቱም የተሟላ አይሆንም፡፡ ምክንያቱም አንድ ሕዝብ ለአገሩ ክብር፣ ለሃይማኖቱ ፍቅር፣ ለማኅበራዊ እሴቱ ዋጋ ከሌለው ማልማትም ማደግም አይችልምና፡፡

እስካሁን ያየናቸው በልማት ስም የተሠሩት ሥራዎች ደግሞ ውስጣቸው ቤተ ክርስቲያንን የማፍረስ ሴራ ያነገቡ የራስን አስተሳሰብና እምነት በሌ ሎች ላይ ለመጫን ዓላማ ያደረጉ ናቸው፡፡ ይህ ዓይነቱ አካሔድ ግን ፍትሐዊም ሃይማኖታዊም አይደለም፡፡ ልማትን እንደ መሸፈኛ ተጠቅመው የቀረቡት ከላይ የጠቀስናቸው ተግባራትም በቤተ ክርስቲያን ላይ የተነጣጠሩ የጥፋት ተልእኮዎች እንጂ አማናዊ ልማቶች ስላልሆኑ ዝም ተብለው መታየት የለባቸውም፡፡
ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ጋዜጣ፣ 23ኛ ዓመት ቁጥር 3፣ ቅጽ 23 ቁጥር 331፣ ከጥቅምት 16-30 ቀን 2008 ዓ.ም

Wednesday, 11 November 2015

መፈተን

የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ እወቁ፡፡ያዕ1፡2

እነዚህ ለማሳያነት በተጠቀሱት የማኅበሩ ተግዳሮቶች መነሻነት በአንዳንድ ግለሰቦች አማካይነት መዋቅሮችን አላግባብ በመጠቀም የግለሰቦቹን ምኞት ከግብ ለማድረስ የሚሠሩና ጥንቃቄ ያልታከለባቸው እርምጃዎች እንጂ የቤተ ክርስቲያን ወይም የመንግሥት ውሳኔ ነው ብለን አናምንም፡፡ ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን አካል እንደመሆኑ ፈተና ስለማይለየው ስለሚያጋጥሙት ፈተናዎች በጸሎት፣ የሚመለከታቸው አካላት በማስረዳትና በመወያየት፣ እንዲሁም በመታገስ አልፎ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሰረተችውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እግዚአብሔር እስከፈቀደበት ጊዜ ድረስ ያገለግላል፡፡

ማኅበሩ ፈተና ሲያጋጥመው መንፈሳዊ ማኅበር እንደመሆኑ መፍትሔ ለማግኘት የሚሄድባቸው መንገዶች ሁልጊዜም የታወቁ ናቸው፡፡ ችግሮች ሲመጡ ጊዜያዊና በእግዚአብሔር ኃይል በቀላሉ ሊፈቱ የሚችሉ መሆናቸውን በመረዳት በጥበብና በትዕግስት ከሚመለከከታቸው አካላት ሁሉ ጋር እየተወያየ ይፈታል፡፡ የችግር አፈታቱ ሥርዓት መንፈሳዊነትን የተከተለ በመሆኑ ሥጋዊ አስተሳሰብን ሳይጨምር ሃይማኖታዊ ፈተና ሲመጣ ማሸነፊያው ሃይማኖታዊ ኃይል ነው ብሎ ያምናል፡፡ እርሱም እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጎ በጾምና በጸሎት በትዕግስትና በጽናት፤ እግዚአብሔርን በመጠየቅ ነው፡፡

በማርቆስ ወንጌል ላይ እንደምናገኘው፡- (ማር. 4፡37) “ብርቱ ዐውሎ ነፋስም ተነሣና ውኃ በታንኳይቱ እስኪሞላ ድረስ ማዕበሉ በታንኳይቱ ይገባ ነበር። እርሱም በስተኋላዋ ትራስ ተንተርሶ ተኝቶ ነበር፤ አንቅተውም። መምህር ሆይ፥ ስንጠፋ አይገድህምን? አሉት። ነቅቶም ነፋሱን ገሠጸው ባሕሩንም። ዝም በል፥ ፀጥ በል አለው። ነፋሱም ተወ ታላቅ ፀጥታም ሆነ። እንዲህ የምትፈሩ ስለ ምን ነው? እንዴትስ እምነት የላችሁም? አላቸው። እጅግም ፈሩና። እንግዲህ ነፋስም ባሕርም የሚታዘዙለት ይህ ማን ነው? ተባባሉ።” ይላል፡፡ በታንኳይቱ የተመሰለችው ቤተ ክርስቲያን በፈተና ልትናወጥ ትችላለች፡፡ እንዲህ ባለ ጊዜ በውስጧ ያለውን፣ ነገር ግን እኛ የድርሻችንን እስክንወጣ ድረስ የሚጠብቀውንና ዝም ያለ (የተኛ) የሚመስለውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በጸሎት መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ፈተናን ጸጥ የሚያደርግ አምላክ እንደምናመልክ ልንዘነጋ አይገባምና ፡፡

ማኅበሩ በቤተክርስቲያንም ሆነ በማኅበራችን ዙሪያ ስላሉ ነገሮች ማንኛውንም መረጃ የሚያስተላልፈው በራሱ ሚዲያና በመተዳደሪያ ደንቡ መሠረት ሥርዓት ባለው መልኩ በሚመለከታቸው የማኅበሩ ኃላፊዎች በኩል እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በሆነ መንገድ የሚተላለፍ ልዩ ልዩ መረጃዎችንና ሀሳቦችን በመያዝ ማኅበሩን በተመለከተ የግል ሀሳብንና ተግባርን ማንጸባረቅ አግባብ አለመሆኑን ሁሉም አካላት ሊያውቀው ያስፈልጋል፡፡
ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ዓላማን ግብ ያለው በመሆኑ በጊዜው በሚታዩ ጥቅመኞችና አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ሁከት ሳንዘናጋ የወንጌል ተልእኳችንን በጥበብና በትዕግስት ከግብ ማድረስ ይገባናል እንላላን፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ያዕቆብ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ እወቁ፡፡ ያዕ.1፡2 እንዳለ ስለ እምነታችንና ስለቤተ ክርስተያናችን የምናደርገውን አገልግሎት ፈታኙ ዲያብሎስ ሊያደናቅፍ ሠራዊቶቹን ቢያሰማራም እግዚአብሔር አምላካችንን ትዕግስትንና ጽናትን እንዲሰጠን ፈተናውንም እንዲያሳልፍልን በጽናት እንለምነው፡፡- እርሱ በሰው ዘንድ የማይቻለውን እንድንችል ማድረግ ያውቅበታልና፡፡ ለዚህም የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ይርዳን፡

Monday, 9 November 2015

EOTC - TV: ነገረ ድኅነት - በቅዱስ መፅሃፍ አስተምኅሮ መሰረት የትኛውን ስናደርግ ነው የምንድነው?

ለአረሙ እንድከም ወይስ ለእህሉ?

እህል ወይስ አረም ?

         በዲያቆን ዳንኤል ክብረት
አሁን ባለንበት ዘመን ያለን የኢትዮጵያ ትውልድ የሀገራችንን ታሪክ፣ የሕዝቦች የእርስ በርስ ግንኙነትና የመሪዎቻችንን ሁኔታ ስንነጋገርና ስንጽፍ በአብዛኛው አሉታዊውን ነገር ይበልጥ ጎልቶ እንዲወጣ፣ ጥላቻ እንዲበቅል፣ ቂም እድሜ እንዲያገኝ፣ ልዩነት እንዲሰፋ፣ ጠብም ሥር እንዲሰድ በማድረግ ላይ የተመሠረተ ሆኖ ይታያል፡፡ ርግጥ ነው በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ የተፈጠሩ የመስተጋብር ችግሮች ሁሉ በኛም ሀገር ተፈጥረዋል፡፡ በኛ ሀገር የተፈጠሩትም በሌሎች ይገኛሉ፡፡ በዓለም ሕዝቦች ታሪክ ውስጥ የኩራትም የውርደትም፣ የፍቅርም የጠብም፣ የሰላምም የጦርነትም፣ የእኩልነትም የጭቆናም፣ የመረዳዳትም የመጠፋፋትም፣ የሥልጣኔም የስይጣኔም ታሪኮች አሉ፡፡ እንኳን በአንድ ሀገር የሚኖሩ የተለያየ ዘውግ፣ ቋንቋ፣ እምነትና የኑሮ ደረጃ ያላቸው ቀርተው በተመሳሳይ ቋንቋ፣ ባሕልና የኑሮ ደረጃ የሚገኝ የአንዲት ሀገር አንድ ወጥ ሕዝብ እንኳን በውስጡ ጽጌረዳም እሾህም አለው፡፡ 

የሚገርመው ነገር ኢትዮጵያን ከዓለም የተለየች የሚያደርጋት ምን እንደሆነ አለመታወቁ ነው፡፡ ኢትዮጵያኮ ሲኦልም አልነበረችም መንግሥተ ሰማያትም አልነበረችም፡፡ ሀገር ነበረች፣ አሁንም ሀገር ነች፡፡ ሀገር የሚገጥማት ፈተና ሁሉ ገጥሟታል፤ ሀገር የሚኖራት ጸጋ ሁሉ ታድሏታል፡፡ በአንዳንድ የታሪክ ምእራፏ ለመንግሥተ ሰማያት ጠጋ፣ በሌላው ምእራፏ ደግሞ ለሲኦል ጠጋ ብላ ይሆናል እንጂ፣ ፈጽማ ሲኦልና መንግሥተ ሰማያት ሆና አታውቅም፡፡ እኛ ልጆቿ ግን ወደ መንግሥተ ሰማያት ጠጋ ማለት ብቻ ሳይሆን ምድራዊት መንግሥተ ሰማያት ብትሆንልን እንወዳለን፤ ለዚያም እንሠራለን፡፡ ወደዚያ በተጠጋችበት ታሪክም እንኮራለን፤ ወደ ሲኦል ለመውረድ አዘንብላ የነበረችበትንም ዘመን ስናስብ በልብ ስብራት እንመታለን፡፡
የታሪክ ሂደት ያመጣቸውን የትናንት ነገሮች ዛሬ አንቀይራቸውም፡፡ ሆነዋልና፡፡ ነገር ግን እንማርባቸዋለን፤ ከትናንት ወስደንም ለዛሬ እንጠቀምባቸዋለን፡፡ የዛሬ ማንነታችን መገንቢያም እናደርጋቸዋለን፡፡ በተቃራኒውም ያለፉትን ዘመናት ጠባሳዎች እየነካካን ቂምን ማመርቀዝ፣ ጥላቻን ማጎንቆል፣ ልዩነትን ማስፋት፣ ፍቅርንም ማደብዘዝ እንችላለን፡፡ ሁለቱም በእኛ ምርጫ ላይ የተመሠረቱ ናቸው፡፡ ምርጫው ለእህሉ ወይስ ለአረሙ ትለፋለታለህ? የሚለው ነው፡፡ 
ታሪካቸውን ለዕድገታቸውና ለሰላማዊ መስተጋብራቸው የተጠቀሙት ግን ከአረሙ ይልቅ ለእህሉ ጊዜና ጉልበታቸውን ያፈሰሱት ናቸው፡፡ ገበሬ ዓመት በሙሉ የሚለፋው አረም ለማብቀል አይደለም፡፡ አረም ለመብቀል ምርጥ ዘር፣ ማዳበሪያ፣ ጉልጓሎ፣ አያስፈልገውም፡፡ ወንፈልና ደቦ አይሰበስብም፡፡ ጉልበትና ጊዜውን አያባክንም፣ ወዝና ላቡን አያንጠፈጥፍም፡፡ ለአረም አንድ ነገር በቂ ነው፡፡ ስንፍና ብቻ፡፡ ገበሬ ከሰነፈ ምንም ሳይደክም አረም እርሻውን ከዳር ዳር ይወርስለታል፡፡ በሬ ሳይጠምድ፣ እርሻ ሳይውል፣ ሌሊት ሳይነሣ፣ ማታ ሳይገባ፣ ዝናብ ሳይመታው፣ ፀሐይ ሳይከካው፣ ብርድ ሳይገርፈው፣ ወላፈን ሳይጠብሰው አረም እንዲሁ ይበቅልለታል፡፡ ገበሬ ለአረም አይለፋም፡፡
የገበሬን ጥበብ፣ የገበሬን ድካም፣ የገበሬን ጉልበት፣ የገበሬን ማዳበሪያ፣ የገበሬን ትዕግሥት፣ የገበሬን ሐሞት፣ የገበሬን ልምድ፣ የገበሬን  ጊዜ፣ የሚፈልገው እህሉ ነው፡፡ ወንፈልና ደቦ የሚሰበስበው ለእህሉ ሲል ነው፡፡ በሬ የሚጠምደው፣ ሞፈር የሚቆርጠው፣ ቀንበር የሚነድለው፣ ጎተራ የሚያዘጋጀው፣ አውድማ የሚለቅልቀው ለእህሉ ሲል ነው፡፡ አረም በስንፍና የሚበቅለውን ያህል እህል የሚበቅለው በጉብዝና ነው፡፡ እህል ያለ ገበሬው ጥበብ፣ ዕውቀት፣ ጉልበትና መሣሪያ ከምድር አይወለድም፡፡ አረም ግን አዋላጅ አይፈልግም፡፡ አረም በራሱ ተወልዶ በራሱ ያድጋል፡፡   
በታሪክ መስክ ላይ የተሠማራ ትውልድም ጊዜውን ማጥፋት፣ ጉልበቱን መሠዋት፣ ጥበቡን ማፍሰስ፣ ዕውቀቱን መከስከስ፣ ያለበት ለአረሙ አይደለም፡፡ ጥላቻው፣ ቂም በቀሉ፣ መቆራቆሱ፣ መናከሱ፣ መለያየቱ፣ መጠፋፋቱ፣ ይኼ የትውልድ አረም ነው፡፡ በስንፍና ብቻ ሊበቅል የሚችል፡፡ በታሪካችን ውስጥ በቅሎ የነበረው እህል ፍቅራችን ነበረ፣ አንድነታችን ነበረ፣ መዋለዳችን ነበረ፤ መዋሐዳችን ነበረ፤ ሥልጣኔያችን ነበረ፤ ጀግንነታችን ነበረ፤ ነጻነታችን ነበረ፡፡ ትኩረታችንን እህሉ ላይ ካደረግነው አረሙን እንቋቋመዋለን፡፡ መቋቋምም ብቻ ሳይሆን እናጠፋዋለን፡፡ አረሙን ማጥፋት ያለብን አረም ስላልነበረ አይደለም፣ አረምን ለመሸፋፈን ሲባልም አይደለም፡፡ አረም ስለማይጠቅመን ነው፡፡ በሀገራችን እንክርዳድ የተሰኘው አረም ሳይለቀም ቀርቶ ከስንዴ ጋር ገብቶ ጠላ የሆነ እንደሆነ ያሳብዳል፡፡ ለዚህም ነው፡-
እንክርዳድ እንክርዳድ የተንከረደደ
ስንዴ መስሎ ገብቶ ስንቱን አሳበደ
የተባለው፡፡
አሁን አሁን በሀገራችን ጉልበታችንን እየጨረስን ያለነው አረሙን ለማብቀል ይመስላል፡፡ አንዲት ጽጌረዳን ከማብቀልና ፈንድታ አበባዋ ሠፈሩን እንዲያውድ ከማድረግ ይልቅ አንድ ማሳ ሙሉ አረም ማብቀል በጣም ቀላል ነው፡፡ አረሙ ስንፍናን ብቻ ይጠይቃልና፡፡ ጽጌረዳዋን ለማብቀል ግን ከመሬቱ፣ ከሰማዩ፣ ከአየሩ፣ ከአራዊቱ፣ ከአላፊ አግዳሚው ጋር መጋደልን ይጠይቃል፡፡  
በታሪካችን ውስጥ የነበረውን እህል ዘሩን አምጥተን መዝራት፣ ዘርተን መከባከብ፣ ተከባክበንም ማሳደግ ይገባን ነበረ፡፡ ጥበባችንን፣ ዕውቀታችን፣ ገንዘባችንንና ጉልበታችንን ለእርሱ ማፍሰስ ይገባን ነበረ፡፡ አሁን ግን ድርሰቶቻችንን፣ ሚዲያዎቻችንን፣ ሐውልቶቻችንን፣ ትርክቶቻችንን፣ ዲስኩሮቻችንን፣ ንግግሮቻችንን፣ የፖለቲካ ፕሮግራሞቻችንን የምናባክነው አረሙን ለማብቀል ሆኗል፡፡ አረምኮ ይህንን ሁሉ አይፈልግም ነበር፡፡ አረምን ለማብቀል ሥርዓተ ትምህርት መቅረጽ፣ ዩኒቨርሲቲ መገንባት፣ የፖለቲካ ፓርቲ ማደራጀት፣ ሚዲያ መዘርጋት፣ ብዕርና ወረቀት ማባከን፣ ምስትርናና ዱክትርና መድረስ አያስፈልግም ነበረ፡፡ አረም እንዲሁ ይበቅላልኮ፡፡
የፖለቲከኞቻችን ብስለት፣ የምሁሮቻችን ብቃት፣ የትውልዱ ምጥቀት፣ የተቋሞቻችን ሥልጠት፣ የሐሳቦቻችን ጥልቀት፣ የሚዲያዎቻችን ፍጽመት፣ የሥልጣኔያችን ርቀት፣ የጥበበኞቻችን ልህቀት የሚታወቀው ባበቀልነው እህል እንጂ ባበቀልነው አረም ብዛት አይደለም፡፡ ለአረምማ እነዚህ ሁሉ አያስፈልጉትም፡፡ እነዚህ ያስፈለጉት ሲቻል አረሙን ቀድሞ ለመከላከል፣ ካልሆነም የበቀለውን አርሞ እህሉን አህል ለማድረግ ነበር፡፡ ለማስተማር እንጂ ለማደንቆር ምን ትምህርት ቤት ይሻል? ለማዳን እንጂ ለማሳመም ምን ሆስፒታል ያስከፍታል? ለፍትሕ እንጂ ለወንጀል ምን ዳኝነት ያስፈልጋል? ለመግባባት እንጂ ላለመግባባት ምን ቋንቋ ያስፈልጋል? ለልዕልና እንጂ ለውርደት ምን ኪነ ጥበብ ያሻል? ለዓለም ዓቀፋዊ እሴቶች እንጂ ለጎጠኝነት ምን ጥበብ መፍሰስ ያሻዋል? ለማጥገብ እንጂ ለማስራብ ምን ፖሊሲ ያስፈልጋል? ለሥልጣኔ እንጂ ለስይጣኔ ምን ፓርቲ ማቋቋም ያስፈልጋል? ለጽድቅ እንጂ ለኃጢአት ምን የእምነት ተቋም ያሻል?
የኛ ጥበብ፣ ዕውቀት፣ ገንዘብና ጉልበት አረም ላይ እየፈሰሰ ነው፡፡ የገበሬ ጉብዝና በአረም ብዛት እንደማይለካው ሁሉ የትውልድ ጉብዝናም በአረም አይለካም፡፡ ‹እንኳንስ ዘንቦብሽ እንዲያውም ጤዛ ነሽ› እንዲሉ እንኳንና የእኛ ጥበብና ገንዘብ፣ ጉልበትና ጊዜ ተጨምሮበት አረም በራሱም ሀገር ያጠፋል፡፡
እንዲህ እርሻው ሁሉ አረም እስኪወርሰው
የለም ወይ፣ የለም ወይ፣ የለም ወይ ባገር ሰው
ተብሎ የለ፡፡
አረም አያዋለዱ ሀገርን ለማሠልጠን መመኘት፣ ተኩላን እያረቡ የበግ ሥጋን እንደመመኘት ያለ ነው፡፡
በገበሬዎቻችን ታሪክ ውስጥ በ16ኛው መክዘ በሀገራችን ተከስቶ በነበረው የሃይማኖት ጦርነት ጊዜ ከ20 ዓመታት በላይ ገበሬው ተረጋግቶ በእርሻ ላይ ስላልነበር አገሩን አረም ወርሶት ነበር ይባላል፡፡ በዚያ ጊዜ ከሀገራችን ገጽ የጠፉ የእህል ዓይነቶች አሉ፡፡ ለዘር ተብሎ የተቀመጠው ወይ በቀጠና ምክንያት ተበልቶ፣ አለያም ቤቱ ሲቃጠል ተቃጥሎ፣ ካልሆነም የተቀበረበት ቦታ በዘመን ብዛት ጠፍቶ ሳይተኩ የቀሩ የእህል ዘሮች አሉ፡፡ የካሕሳይ ገብረ እግዚአብሔርን ኅብረ ብዕር ያነበበ ሰው ከሚያያቸው የእህል ዘሮች መካከል ብዙዎቹ ስማቸውን ትተው ጠፍተው የቀሩት እንዲህ ባሉ ዘመናት ነው ይባላል፡፡ አረሙ ግን አልጠፋም፡፡ እንዲያውም ተመችቶት ነበር፡፡
በታሪካችንም ውስጥ እየጠፉና እየመነመኑ የመጡ በጎ እሴቶች፣ ባሕሎች፣ ልማዶችና ወጎች አሉ፡፡ አገር ችግር ላይ ስትወድቅ እህሉን የሚያመርተው ሲያጣ፣ ዘሩ ይጠፋል፡፡ ያንን ዕድልም አረሙ ይጠቀምበታል፡፡ ምድሩም እህል ተዘርቶበት የማያውቅ ይመስላል፡፡  
አሁን ለዚህ ትውልድ ጥያቄው አንድ ነው፤ ለአረሙ እንድከም ወይስ ለእህሉ? እህሉን በማምረት ብርታትህን ታሳያለህ ወይስ አረሙን በማብቀል ስንፍናህን? የኢትዮጵያ መልክ የሚቀየረው ለዚህ ጥያቄ በምንሰጠው መልስ ነው፡

"ሉቃስ ከ12ቱ ሃዋርያት ሳይሆንቱ ከ72 አርድት ነው"

ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ
ጥቅምት 24 ቀን 2008 ዓ.ም ___በዲ/ን ኃይለ ማርያም አስፋው
ሉቃስ ማለት በላቲኑ ትርጓሜ ብርሃናማ፣ ብርሃን የያዘ ማለት ነው፡፡ በትርሜ ወንጌል የተሰጠው ትርጉም ደግሞ ሉቃስ ማለት ዓቃቤ ሥራይ (ባለ መድኃኒት) ማለት ነው፣ ቀድሞ ዓቃቤ ሥራይ ዘሥጋ (ሥጋዊ ሐኪም) ነበር በኋላ ግን ዓቃቤ ሥራይ ዘነፍስ ( መንፈሳዊ ሐኪም) ሆኖአልና፡፡ አንድም ተንሣኢ (ፈጣን) ማለት ነው ለስብከተ ወንጌል ይፋጠናልና፣ አንድም መበሥር (ብሥራ ነጋሪ) ማለት ነው ብሥራተ መልአክን ይጽፋልና በማለት ይተረጉመዋል፡፡የተወለደው በሶርያ አንጾኪያ ነው፡፡ የአሕዛብ ወገን የነበረና በኋላም ወደ ክርስትና እንደተመለሰ ታሪኩን የጻፉ ይናገራሉ፡፡ ቅዱስ ሉቃስ አይሁዳዊ ሳይሆን ወንጌልን የጻፈ ወንጌላዊ ነው፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ከሰባ ሁለቱ አርድዕት ነው የሚቆጠረው፡፡

ቅዱስ ሉቃስ የተወደደ ሐኪም ነበር፡፡ ለዚህም ማረጋገጫው ቅዱስ ጳውሎስ በቆላስይስ መልእክቱ ም.4፡14 የተወደደው ባለ መድኃኒቱ ሉቃስ ዴማስም ሰላምታ ያቀርቡላችኋልበማለት ገልጦታል፡፡ በወንጌሉም አጻጻፍ ላይ ስለ ሕመማቸውና ድኅነት ስለሚያገኙበት ሁኔታ ገልጦ ጽፏል፡- ስለ ደጉ ሳሚራዊ ሉቃ 10፡30-35፣ ደም ይፈሳት ስለነበረችው ሴት ሉቃ8፡43

ቅዱስ ሉቃስ ሠዓሊ ነበር፡፡ ይህ ሞያው ወንጌሉ ሲጽፍ ሥዕላዊና ገላጭ በሆነ መልኩ ለመጻፍ ረድቶታል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ትውፊት እንደሚናገረው የቅድስት ድንግል ማርያም ምስለ ፍቁር ወልዳ ለመጀመርያ ጊዜ የሳለው እርሱ ነው፡፡እነዚህም ሥዕሎች በኢትዮጵያ ውስጥ በተድባበ ማርያም' በደብረ ዘመዳ' በዋሸራ'በጅበላ ይገኛሉ፡፡

ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በሰዓታት ምስጋናው መልክአ ሥዕል ላይ ሰላም ለሥዕልኪ እንተ ሠዐላ በእዱ ሉቃስ ጠቢብ ዘእም ወንጌላውያን አሐዱ ከወንጌላውያን አንዱ የሆነው ጠቢቡ ሉቃስ ለሣላት ሥዕልሽ ሰላምታ ይገባል እያለ እመቤታችንን አመስግኖአታል፡፡

ቅዱስ ሉቃስ ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር የተገናኘው በአንጾኪያ ነው፡፡ ከዚያ በኃላ ተወዳጅ ደቀ መዝሙር ሆነ፡፡ በ2ኛ ጢሞ 4፡11 ሉቃስ ብቻ ከእኔ ጋር አለ፣ እንዲሁም ፊል 1፡24 ላይ አብረውኝም የሚሠሩ ማርቆስና አርስጥሮኮስ ዴማስም ሉቃስም ሰላምታ ያቀርቡልሃል ብሎ እንደገለጠው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ሰማዕትነት እስኪቀበል ድረስ ከርሱ ጋር እንደነበር በሐዋርያት ሥራ መጽሐፉ ገልጧል፡፡ ከቅዱስ ጳውሎስ በፊት የቅዱስ ዮሐንስ ደቀ መዝሙር እንደነበረ ትርጓሜ ወንጌል ላይ ለዮሐንስ ምድረ ፅርዕ ደረሰችው፣ ለሰብዓ አርድእት ግን ዕጣ የላቸውም፡፡ አንዱም ሁለቱም ሆነው አንዱን ሐዋርያ አንዱም ሁለቱም ሆነው አንዱን ሐዋርያ ተከትለው ይሄዳሉ ሉቃስም ዮሐንስን ተከትሎ ይሄዳል፡፡ መቄዶንያ የምትባል ሀገር ከፍሎ አስተምር ብሎ ሰጥቶታል፡፡

የሠለሥቱ ሐዲሳት መቅድም ደግሞ እንዲህ ይገልጠዋል ለሰብዓ አርድዕት ዕጻ የላቸውም አንዱም ሁለቱም አንዱን ሐዋርያ እየተከተሉ ይሄዳሉ ሉቃም ዮሐንስን ተከትሎ ሔዷል፣ ከሀገረ ስብከቱ ከፍሎ መቄዶንያ የምትባል ሀገር አስተምር ብሎ ሰጥቶታል፡፡ ከዚያ ገብቶ ጌታ ከፅንስ ጀምሮ ያስተማረውን ትምህርት የሠራውን ትሩፋት፣ ያደረገውን ተአምራት ቢነግራቸው ከገቢረ ኃጢያት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከአምልኮ ጣዖት ወደ አምልኮ እግዚአብሔር ተመለሱ አመኑ ተጠመቁ፡፡ ትምህርት ካልደረሰበት ለማዳረስ በሚሄድበት ጊዜ ታዖፊላ መኮንነ እስክንድርያ ይለዋል በርሱ ስብከት አምኖ ዜና ሐዋርያትን ጻፍልኝ ብሎት ጽፎለታል፡፡ አጻጻፉ አምስት ወገን ነው፤ ጌታ እንዳረገ መቶ ሃያው ቤተሰብ ባንድነት እንደ ነበሩ ይሁዳ እንደወጣ፣ በእግሩም ማትያስ እንደገባ፣ ባድነት ሳሉም መንፈስ ቅዱስ እንደ ወረደላቸው፣ በኢየሩሳሌም የነበሩ አይሁድ እስጢፋኖስን በድንጋይ ወግረው እንደገደሉት ይልቁንም መምህሩ ቅዱስ ጳውሎስ ከእምነት እስከ ሞቱ ያስተማረውን ትምህርት የሠራውን ትሩፋት ያደረገውን ተአምራት ጻፍልኝ ብሎት ጽፎለታል:: ጥቅምት 22 በሚነበበው ስንክሳር የቅዱስ ጴጥሮስም ደቀ መዝሙር እንደነበር ተገልጧል፡፡

ቅዱስ ሉቃስ ከሰማንያ አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሁለት መጻሕፍት አሉት፡፡ እነሱም የሉቃስ ወንጌልና የሐዋርያት ሥራ ናቸው፡፡ቅዱስ ወንጌሉን የጻፈው በአካይያ (በሮም 62-63 ዓ.ም ጻፈው የሚሉም አሉ) 58-60 ዓ.ም ሲሆን የጻፈበት ቋንቋ ፅርዕ ነው፡፡ የአጻጻፍ ስልቱ 'የትርጉም አጠቃቀሙ' የታሪክ ሂደቱ ሲታይ ቅዱስ ሉቃስ የተማረ ሊቅ እንደነበር ያስረዳል፡፡ ሲጽፍም የከበርህ ቴዎፍሎስ ሆይ፥ ከመጀመሪያው በዓይን ያዩትና የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት እንዳስተላለፉልን፥ በኛ ዘንድ ስለ ተፈጸመው ነገር ብዙዎች ታሪክን በየተራው ለማዘጋጀት ስለ ሞከሩ፥ እኔ ደግሞ ስለ ተማርኸው ቃል እርግጡን እንድታውቅ በጥንቃቄ ሁሉን ከመጀመሪያው ተከትዬ በየተራው ልጽፍልህ መልካም ሆኖ ታየኝ በማለት እርግጠኛ ሆኖ ነው፡፡ ይህ አገላለጡ ቅዱስ ሉቃስ የታሪክ ሰው ነበር ያሰኛል፡፡ ሁለቱንም መጻሕፍት ማለትም ወልጌሉንና የሐዋርያት ሥራ ራሱ እንደጻፈው በማያሻማ መልኩ በወንጌሉ መጨረሻና በሐዋርያት ሥራ መጀመርያ ላይ የተጠቀመው አገላለጽ በማየት መረዳት ይቻላል፡፡ ወንጌሉ በእርገት ሲጨርስ €™እስከ ቢታንያም አወጣቸው እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው፣ ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማይም ዐረገ። እነርሱም፤ ሰገዱለትና በብዙ ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፥ዘወትርም እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እየባረኩ በመቅደስ ኖሩ።ሉቃ 24፡50-53 በማለት ሲሆን የሐዋርያት ሥራ ሲጀምር ቴዎፍሎስ ሆይ፥ ኢየሱስ የመረጣቸውን ሐዋርያትን በመንፈስ ቅዱስ ካዘዛቸው በኋላ እስከ ዐረገበት ቀን ድረስ፥ ያደርገውና ያስተምረው ዘንድ ስለ ጀመረው ሁሉ መጀመሪያውን ነገር ጻፍሁ፤ደግሞ አርባ ቀን እየታያቸው ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት ነገር እየነገራቸው፥ በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለእነርሱ ራሱን አሳያቸው። ከእነርሱም ጋር አብሮ ሳለ ከኢየሩሳሌም
እንዳይወጡ አዘዛቸው፥ ነገር ግን። ከእኔ የሰማችሁትን አብ የሰጠውን የተስፋ ቃል ጠብቁ የሐ.ሥራ 1፡1-4 በማለት ነው፡፡

የቅዱስ ሉቃስ ወንጌል ከሦስቱ በተለየ መልኩ ታሪካዊና ስዕላዊ በሆነ መልኩ በተለይ ከአይሁድ ውጪ ያሉትና አሕዛብ ሊረዱት በሚችሉ መልኩ የተጻፈ ነው፡፡ በዘመኑ ከነበረው የአይሁድ ስለ ሴቶች ከነበራቸው አመለካከት ወጣ ባለ መልኩ ስለ ሴቶች አጉልቶ በስፋት የጻፈ ወልጌልዊ ነው ፡፡በተጨማሪም ስለ መንፈስ ቅዱስ ጸጋ፤ ስለ ጸሎት ፤ስለ ርኅራኄ ፤ስለ ሀብታምና ድሃ በሰፊው የጻፈ ወንጌላዊ ነው፡፡ በሐዋርያት ሥራ መጽሐፉ ስለ ቤተክርስቲያን' ስለ አንድነት' የሐዋርያነት መሠረት' ዓላማ' ትጋት' ማሸነፍ' ስለ ሌላው መጨነቅ' ኃላፊነትን ስለመወጣት'ተጋድሎን'በተግባር በሚታይና በሚጨበጥ ማስረጃ የጻፈ ሐዋርያ ነው፡፡

ቅዱስ ሉቃስ የሚመሰለው በገጸ ላህም ነው፡፡ምክንያቱም አምጽኡ ላሕመ መግዝዓ ወጥብሑ ንብላእ ወንትፌሣሕ ምስሌሁ (ፍሪዳ አምጡና እረዱ ከእርሱ ጋር እየበላን ደስ ይበለን) ሉቃ.15፤23 እያለ€™ ምሳሌውን ይጽፋልና፡፡ አንድም በጤግሮስ ይመሰላል ጤግሮስ ፈለገ መዓር (የመዓር ወንዝ) ነው ርስትነቱም ጸዊረ ነገር (ምሥጢር መሸከም) የሚቻላቸው ሰዎች ርስት ነው፡፡ ሉቃስም አባ ሥረይ ሎሙ እስመ በዘኢየአምሩ (አባት ሆይ የሚሠሩትን አያውቁምና ይቅር በላቸው) ይገብሩ' በትዕግሥትክሙ ታጠርይዋ ለነፍስክሙ (በመታገሳችሁ ነፍሳችሁን ገንዘብ ታደርጋላችሁ) እያለ ክቡድ ክቡድ ነገር ይጽፋልና፡፡

ቅዱስ ሉቃስ በድንግልና የኖረ ሐዋርያ ነው፡፡ በግሪክ ብዙ ሐዋርያዊ አገልግሎት ፈጽሟል፡፡ ያረፈውም በቆስጠንጢኖስ 2ኛ ዘመን በ84 ዓመቱ በሰማዕትነት ነው፡፡ ቅዱስ አጽሙ በ357 ወደ ቁስጥንጥንያ የፈለሰ ሲሆን ከቁስጥንጥንያ ወደ ጣልያን ፑዳ በ1177 ዓ.ም በድጋሚ ፈልሷል፡፡

ስለ እረፍቱም ጥቅምት 22 ቀን የሚነበበው ስንክሳር እንዲህ ይተርካል:: ቅዱሳን ጴጥሮስና ጳውሎስ ከተገደሉ በኋላ በሮም ሀገር የሚያስተምር ሆነ በቀናች ሃይማኖትም ይጸኑ ዘንድ ለምእመናን መልእክትን ይጽፍ ነበር ስለዚህም ጣዖት አምላኪዎች ከአይሁድ ጋር በመስማማት በአንድ ምክር ተስማሙ በንጉሥ ኔሮን ፊት ቆመው ስለ ሐዋርያው ሉቃስ እንዲህ ብለው ጮሁ ይህ ሉቃስ በሥራይ ብዙ ሰዎችን ወደ ትምህርቱ አስገባቸው አሉ፡፡ ንጉሥ ኔሮንም ወደ ፍርድ አደባባይ ሉቃስን እንዲያቀርቡት አዘዘ ሐዋርያው ሉቃስም ከዚህ ዓለም መውጫው እንደ ደረሰ በመንፈስ ቅዱስ አውቆ ወደ ባሕር ዳርቻ ሔደ በዚያም ዓሣ የሚያጠምድ አንድ ሽማግሌ ሰው አገኘ መጻሕፍቱንና ደብዳቤዎችን ሰጠው ወደ እግዚአብሔር መንገድ መርተው ያደርሱሀልና እሊህን መጻሕፍት ጠብቃቸው አለው፡፡ በንጉሥ ኔሮን ፊትም ቀርቦ በቆመ ጊዜ ንጉሡ በሥራይህ ሕዝቡን የምታስት እስከ መቼ ነው አለው ቅዱስ ሉቃም እኔ ለሕያው እግዚአብሔር ልጅ ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ነኝ እንጂ ሥራየኛ አይደለሁም ብሎ መለሰለት ንጉሥ ኔሮንም ሁለተኛ እንዲህ አለው እየጻፈች ሰዎችን የምታስት ይህች እጅህን እኔ እቆርጣታለሁ ይህንንም ብሎ የቀኝ እጁን እንዲቆርጡት አዘዘ፡፡ በቆረጡትም ጊዜ ንጉሥ ሆይ እኛ የዚህን ዓለም ሞት እንደማንፈራ ዕወቅ ነገር ግን የጌታዬና የፈጣሪዬን ኃይሉን ታውቅ ዘንድ አሳይሃለሁ ይህንንም ብሎ የተቆረጠች የቀኝ እጁን በግራ እጁ አንስቶ ከተቆረጠችበት ቦታዋ ላይ አገናኝቶ እንደ ቀድሞዋ ደኅነኛ አደረጋት ከዚህም በኃላ ለያት በዚያም የነበሩ አደነቁ የሠራዊቱም አለቃና ሚስቱ ብዙዎችም ሰዎች ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ቁጥራቸውም አራት መቶ ሰባ ሰባት ነፍስ ሆነ፡፡ ንጉሡም ከቅዱስ ሉቃስ ጋር ራሶቻቸውን እንዲቆርጡ አዘዘና ቆረጡአቸው የምስክርነት አ
ክሊልም በመንግስተ ሰማያት ተቀበሉ ከዚህም በኋላ የቅዱስ ሉቃስን ሥጋ በማቅ አይበት ውስጥ አድርገው ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ ወደ አንድ ደሴት ደረሰ ምእመናንም አግኝተው ወስደው ገነዙት በአማረ ቦታም አኖሩት ለእግዚአብሔር ምስጋነና ይሁን እኛንም በዚህ ሐዋርያ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡

ሰላም ለሉቃስ እንተ ረትዐ ልሳኑ ወንጌለ መለኮት ይጽሐፍ እምእለ ብዙኃን ወጠኑ፡፡ ከመ ያርኢ ኀይለ ቅድመ ኔሮን ወተዐይኑ አስተላጸቃ ወሌለያ የማኑ ለምትርት እስመ ላዕሌሁ ተሠውጠ ለክርስቶስ ሥልጣኑ፡፡

መስቀል ማለት ምን ማለት ነው?


መስቀል ማለት ምን ማለት ነው?
በዲ/ን ዶ/ር ቴዎድሮስ በለጠ2008 ዓ.ም.
ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና በቃል መነገሩ፣ በኅሊና መዘከሩ፣ በሰው ልብ መታሰቡ፣ በቅዱሳት መጻሕፍት መዘገቡ ከፍ ይበልና፣ ጌታችንንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛ ልጆቹ ፈቃዱን እያደረግን እንድንኖርና እርሱም ከመልካም ምግባራችንና ከበጎ ትሩፋታችን ብቻ የተነሳ ፍጹማን እንደማንሆን ያውቃልና፣ ከማያልቅ ልግስናው ከማይጓደል ምሕረቱ ዘመናትን እየመጸወተን ደስ የሚሰኝበትን ለእኛ እያደረገ በቸርነቱ ያኖረናል:: ከእርሱና ከዓላማው ጋር ጸንተን እንድንኖርም እንዲህ ሲል በቅዱስ ወንጌል አዝዞናል:: “ዘይፈቅድ ይትልወኒ ይጽላዕ ነፍሶ ያጥብዕ ወይንሳዕ መስቀለ ሞቱ ወይትልወኒ (እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር፥ ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ) ወምንተ ይበቁዖ ለሰብእ ለእመ ኩሎ ዓለመ ረብሐ ወነፍሶ ኃጉለ (ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል?)” (ማቴ. 16:24-26)።
ጥንቱንም ቢሆን እኛ የተፈጠርነው በሕይወት እንድንኖር ነው። ትንሳኤና ሕይወት ክርስቶስ ግን የተወለደው ስለኛ እንዲሞት ነው:: በዚህም ሁላችን ለእርሱ እንድንኖር እርሱ ስለ ሁላችን ሞተ "በሕይወትም ያሉት ስለ እነርሱ ለሞተውና ለተነሣው እንጂ ወደ ፊት ለራሳቸው እንዳይኖሩ ስለ ሁሉ ሞተ። "(1ቆሮ፣ 5:15)። ይህ ግን መስቀል የገደለው ያይደለ ይልቁንም በመስቀሉ ሞትን ገደለበት እንጂ:: "በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረደ፥ ለሞትም ይኸውም የመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ሆነ።" (ፊል. 2:8) እንዲል::
ሊከተለኝ የሚወድ ነፍሱን ይጥላ አለ፣ ይህም ነፍሱንና ሥጋውን የሚለይ መከራ ለመቀበል ይጨክን ሲል ነው። ሰውስ ለክርስትና ፍኖቱ ለነፍሱ ሥምረት እያደረ የሥጋውን ፈቃድ እየገፋና እየጠላ ሊኖር ይገባዋል። ለዚህም ጌታችን ተከታዩን ሃሳብ እንዲህ ሲል አስፍሮታል "ወምንተ ይበቁዖ ለሰብእ ለእመ ኩሎ ዓለመ ረብሐ ወነፍሶ ኃጉለ፤ ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል?" መከተሉም ቢሆን ሌጣውን ያይደለ የሞቱን መስቀል ተሸክሞ ይለናል::
መስቀል ምንድር ነው ?
መስቀል በቀደመው ዘመን ለኃጢአተኞች እግዚአብሔርን ለበደሉ መቅጫ የነበረ "በእንጨት ላይ የተሰቀለ በእግዚአብሔር ዘንድ የተረገመ ነውና" (ዘዳ፣21:23)። ነገር ግን በአዲስ ኪዳን ለክርስቲያኖች ኃይል፣ ጽንዕ፣ ቤዛና መድኃኒተ ነፍስ ሆኖ የሚያገለግል አርማ ነው:: ወደዚህ ክብር እንዴት ሊሻገር እንደቻለ ሊያስረዱ የሚችሉ በመስቀሉ ከተፈጸሙ ድንቅ መንክራት እፁብ ተዓምራት መካከል ተከታዮቹን ሦስት ዓበይት ነጥቦች እንደእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ እንመለከታለን::
+ ጠላት የራቀበት ነው።
መስቀል የቀደመው እባብ የዲያቢሎስ ራስ የተቀጠቀጠበት እኛም ድል መንሳትን በግልጥ ያየንበት እጸ መድኃኒት ነው:: "በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው። እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል።አለቅነትንና ሥልጣናትን ገፎ፥ ድል በመንሣት በእርሱ (በመስቀል) እያዞራቸው በግልጥ አሳያቸው።" (ቆላ፣ 2:14) እንዲል።
+ እኛ የቀረብንበት ነው።
ተመልከቱ ራሱን ወደኛ ያቀረበበት ነው አላልንም "አመ ተለአልኩ እምድር እስህብ ኩሎ ኃቤየ፤ እኔም ከምድር ከፍ ከፍ ያልሁ እንደ ሆነ ሁሉን ወደ እኔ እስባለሁ።" (ዮሐ፣12:32) እንዳለ እኛን ወደራሱ አቀረበበት፣ ምክንያቱም ሰው በድሎ ራቀው እንጂ እርሱ ከሰው የተለየበት ጊዜ አልነበረምና። "እኔ የቅርብ አምላክ ነኝ እንጂ የሩቅ አምላክ አይደለሁም።" (ኤር፣23:23) እንዳለን። ይበልጡንም ለተዛምዶ ረቂቅ ቅርበቱ ያይደለ ሥጋችንን ነስቶ አማኑኤል ተሰኝቷል። "እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ።" ይህም በኩነት ታዲያ ዓላማው ወደእኛ መቅረብ ብቻ ቢሆን ይህ ልደቱ በበቃው ነበር። መስቀሉ ግን ወደኛ መምጣቱን ባንቀበል ወደራሱ ሊወስደን ወደ ሰማይ ቤታችን ሊስበን በቀራንዮ ተተከለ። ለዚህም ሊቁ ማር ኤፍሬም "አቅረበነ ኃቤሁ ዘዚአነ ሞተ ነሳ ወእንቲአሁ ሕይወተ ወኃበነ- ወደራሱ አቀረበን የእኛን ሞት ወስዶ የእርሱን ሕይወት ለእኛ ሰጠን" ሲል መነሻችንን ያስረዋል።
+ የጥል ግድግዳ የፈረሰበት
ሰው የሞትን እጽ ቆርጦ ቢበላ አምላኩን በደለ። በዚህም የጸብ ግድግዳ ተተከለ። ሰው ከአምላኩ ተለየ ልዑለ ቃል ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ "ነገር ግን በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፥ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሰውሮታል።" (ኢሳ፣59:2) ሲል እንደገለጸው፣ ታዲያ ከህገ ልቡና ወደ ህገ ኦሪት መሻገሩ ፍጻሜ ያለው ድኅነት ሊያመጣ ባለመቻሉ የሚበልጥና የሚሻል አዲስ ኪዳን የሚሰጥበት አዲስ መስዋዕት የሚሰዋበት አዲስ ድንኳን አስፈለገ (ዕብ፣ 9:11)። ለዚህም የአዲስ ኪዳን ሥርዓት ክቡር ደሙ የፈሰሰበት የሕይወት ህብስት ቅዱስ ሥጋው የተቆረሰበት ዐረፍተ ማእከል የተናደበት እጸ መድኃኒት ቅዱስ መስቀሉ ተሰጠን። "እርሱ ሰላማችን ነውና፤ ሁለቱን ያዋሐደ በአዋጅ የተነገሩትንም የትእዛዛትን ሕግ ሽሮ በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳን በሥጋው ያፈረሰ፤ ይህም ከሁለታቸው አንድን አዲስን ሰው በራሱ ይፈጥር ዘንድ ሰላምንም ያደርግ ዘንድ፥ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው።" (ኤፌ፣ 2:15)።
እንግዲህ በጠቅላላው መስቀል የምንለው፣ በቁሙ ከቤተክርስቲያን ጉልላት እስከ ምዕመናን ንቅሳት የሚታይ የድል ምልክት፣ በሰሌዳ ተስሎ በጣት ተመሳቅሎ የሚገኝ የድኅነት አርማ፣ ካህናት በእጃቸው ይዘው የሚፈቱበት፣ ክርስቲያኖች በአንገታቸው አስረው ማንነታቸውን የሚመሰክሩበት መገለጫ ሲሆን. በሌላ አገባብ መከራ የተጋድሎ ፍኖት ማለት ነው።
እግዚአብሔር ወልድ ክርስቶስ ስለሁላችን መዳን መከራን ተቀብሎልናል። እናስተውል፣ እያንዳንዳችን በመዳን ኑሮ ሐሳባችን፣ እቅድ ምኞታችን በመከራው ልንካፈለው፣ በሞቱ ልንመስለው ፈለጋውን ልንከተለው ይገባናል።
"ስለዚህ ኢየሱስ ደግሞ በገዛ ደሙ ሕዝቡን እንዲቀድስ ከበር ውጭ መከራን ተቀበለ። "(ዕብ፣13:12) እንደተባለ፤ ከበር ውጪ አለ በቀራንዮ ኮረብታ የራስ ቅል በተባለ ጎልጎታ ሊቀድሰን ተሰቀለ። እኛ ክርስቶስ በደረሰበት መከራ ከድቅድቁ ጨለማ ድንቁርና ወደሚደነቀው ብርሃን እውቀት የተሻገርነው፣ ስለ አዳም በደል መከሰስን ጥለን ስለራሳችን ጽድቅ መከራን በመቀበል እንድንከተለው ነው:: ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ "የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና፤ ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሎአልና። "(1ኛ፣ጴጥ.2:21) ሲል እንዳስረዳን። በዚህም ኅሩይ ነዋይ ቅዱስ ጳውሎስ "እርሱንና የትንሣኤውን ኃይል እንዳውቅ፥ በመከራውም እንድካፈል፥ ወደ ሙታንም ትንሣኤ ልደርስ ቢሆንልኝ፥ በሞቱ እንድመስለው እመኛለሁ። "(ፊል.3:10-11)። ሲል ምኞቱን አስረዳን ምን ይጠቅማል? የሚል ቢኖር ልሳነ ዕፍረት እንዲህ ያስረዳዋል "ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን።" (ሮሜ. 6:5)።
ሁሉ የራሱ መስቀል አለው ሸክሙን የሚሸከምበት
"ለሁሉም እንዲህ አላቸው፦ በኋላዬ ሊመጣ የሚወድ ቢኖር፥ ራሱን ይካድ መስቀሉንም ዕለት ዕለት ተሸክሞ ይከተለኝ።" (ሉቃ፣9:23)
ሁሉ የራሱን ሸክም ይሸከማልና
"ወኩሉ ያመክር ምግባሮ (ሁሉ ሥራውን ይመርምር ለሌላው ሳይሆን ለራሱ የሚመካበትን) እስመ ኩሉ ፆሮ ይፀውር (እያንዳንዱ የገዛ ራሱን ሸክም ሊሸከም ነውና)" (ገላ6:5) እንዲል።ስለዚህ የምንሸከመው መስቀላችን የምንሰቀልበት ሳይሆን ሸክማችንን የምንሰቅልበት ነው::"የክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑቱ ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ።" (ገላ፣ 5:24) እንደተባለ።
እስኪ አእምሮአችንን ከመባከን ሰብስበን ነፍሳችንን የሚያሳርፍ አንድ ታሪክ እናንብብ
"እርሱም በመንገድ ሲወጣ አንድ ሰው ወደ እርሱ ሮጦ ተንበረከከለትና። ቸር መምህር ሆይ፥ የዘላለም ሕይወትን እወርስ ዘንድ ምን ላድርግ? ብሎ ጠየቀው።ኢየሱስም፦ ስለ ምን ቸር ትለኛለህ? ከአንዱ ከእግዚአብሔር በቀር ቸር ማንም የለም። ትእዛዛትን ታውቃለህ፤ አታመንዝር፥ አትግደል፥ አትስረቅ፥ በሐሰት አትመስክር፥ አታታልል፥ አባትህንና እናትህን አክብር አለው።እርሱም መልሶ፦ መምህር ሆይ፥ ይህን ሁሉ ከሕፃንነቴ ጀምሬ ጠብቄአለሁ አለው።ኢየሱስም ወደ እርሱ ተመልክቶ ወደደውና። አንድ ነገር ጐደለህ፤ ሂድ፥ ያለህን ሁሉ ሽጠህ ለድሆች ስጥ፥ በሰማይም መዝገብ ታገኛለህ፥ መስቀሉንም ተሸክመህ ና፥ ተከተለኝ አለው።ነገር ግን ስለዚህ ነገር ፊቱ ጠቈረ፥ ብዙ ንብረት ነበረውና እያዘነም ሄደ።" (ማር 10:17)። አይገርማችሁም በምድራችን ላይ ገንዘብን መውደድ የከበደ ሸክም እየሆነባቸው "ገፋኤ-ነዳይ መፍቀሬ- ነዋይ" መጠርያቸው የሆኑ ብዙዎች አሉ:: ፍቅረ ነዋይ (ገንዘብን መውደድ) ለኃጢዓት ሥርና ራስ ነው ...... ጌታችን ተርቦ ሳይሳሳ፣ ተፈትኖ ድል ሳይሆን፣ ለሁላችን አርአያ በሆነበት ገዳመ ቆሮንቶስ ጠላታችንን ድል ከነሳባቸው መንገዶች አንዱ ፍቅረ ነዋይን በጸሊዓ ነዋይ ነበር። ይህም ፍቅረ ነዋይ ርዕሰ-ኃጣውእ ከስስትና ከትዕቢት ጋር አርዕስተ ኃጥውእ እየተባለ ይጠራል። ይሁንና ግን ከአስራ ሁለቱ አንዱ በሆነው የአስቆሮቱ ይሁዳ ልብ ገብቶ ተሳካለት። በዚህ ሥፍራ ደግም የኃጢዓት ሥር ተብሎ ተጠራ "ገንዘብን መውደድ የክፋት ሁሉ ሥር ነውና፥ አንዳንዶች ይህን ሲመኙ፥ ከሃይማኖት ተሳስተው በብዙ ሥቃይ ራሳቸውን ወጉ።" (1ኛ.ጢሞ.6:10) እንዲል። እንግዲህ ይህን የመሰለው ኃጢዓት ሁሉ ክቡድ ሸክም ይባላል። የምሕረት አምላክ ግን በፍቅር ልሳን እንዲህ እያለ ይጠራናል "እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ። ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜም ቀሊል ነውና።" (ማቴ.11:28-30)።
ቀሊል የሆነውን የእርሱን ሸክም እንሸከም ዘንድ እሱ የኛን ክቡድ ሸክም በመስቀል ላይ ተሸከመ:: እንግዲህ ተመልከቱ በዚህ መንገድ እኛም ሕይወታችንን እንድንሰጠው ሕይወቱን ሰጠን ለምን? የሚል ቢኖር እርሱ የብዙዎችን ኃጢዓት በእንጨት ላይ የተሸከመው ብዙዎች የእርሱን ሕይወት በዘመናቸው እንዲሸከሙ ነውና:: ነቢዩ አስቀድሞ በትንቢት እንዲህ እንዳለ "ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ።" (ኢሳ 53:12) ሊቀሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስም የቃሉን መፈስጸም እንዲህ ሲል እንዳስረዳ "ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ፤" (1ኛ.ጴጥ፣2:24)።
መከራን መቀበል (መስቀላችንን መሸከም)
+ ኃጢዓትን (አርእስተ ኃጣውእ) ያስተዋል።
"በሥጋ መከራን የተቀበለ ኃጢአትን ትቶአልና።" (1ጴጥ፣ 4:2)።
+ ወደ እግዚአብሔር ያስገባል።
"ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል" (ሐዋ 14:22) እንደተባለ ለብዙዎች ዘለፋ የሆነው ይህ የቅዱሳን ሐዋርያት ምስክርነት "በጸጋ ድነናል" እያሉ ባልተገባ ፍካሬ ቃሉን እየጠቃቀሱ፤ ለመብልና መጠጥ ይህን ለመሰለው የሥጋ ፈቃድ ራሳቸውን ለሚያስገዙ ጅራፍ ይሆንባቸዋል፤ ምክንያቱም "የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችምና።" (ሮሜ.14:17) ይለናልና::
ማጠቃለያ
ቅዱስ አባታችን ብጹዕ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ በአንድ መጽሐፋቸው "ፈተና ያለው ትምህርት ቤት አይደለም፣ ይልቁንም ትምህርት ቤት ያለው በፈተና ውስጥ ነው" ብለዋል። እኛም እንዲህ እንላለን "ሕይወት በመከራ የተሞላ ነው ለሚል፣ የለም ለክርስቲያንስ መከራ በህይወት የተመላ ነው እንጂ"፤ ሊቁ "መከራ ኢርኅቀ እምርዕሰ ጻድቃን ወርዕሰ ጻድቃን ኢርኅቀ እምነ መከራ ግሩም." ሲል ቅኔውን ይጀምራል። የማይጠፋ ስምና የሕይወትን አክሊል ገንዘብ ሊያደርጉ ሲሹ መከራ አይርቃቸውም። ቢርቃቸውም እንኳ እነርሱ ከመከራ መች ይርቁና። መክበርያቸውን ሽተው ራሳቸው ላይ ተጋድሎ ያጸናሉ ሌላውም ሊቅ የጸናውን ሰማዕት ተመለከተና "ኦ ጊዮርጊስ ስቃየ ኮንከ ለሥቃይከ" ሲል አደነቀ እንዴት ባለ መከራ እንዲገድሉት ይጨንቃቸው የነበሩ አላውያን ቢፈጩት፣ ቢያቃጥሉት፣ አመድ አድርገው ቢበትኑት "እነሆኝ የክርስቶስ ባርያ" እያለ ሞትን ድል ቢነሳና ከመካከላቸው ቢገኝ ለስቃዩ ስቃይ ሆነበት ወይግሩም! ታዲያ የቀደሙ ምስክሮች ሕይወት ይህ ከነበረ የእኛ ተጋድሎ ወዴት ይሆን? "ጻድቅም በጭንቅ የሚድን ከሆነ ዓመፀኛውና ኃጢአተኛው ወዴት ይታይ ዘንድ አለው?" (1ኛ.ጴጥ.4:18)።
እንግዲህ በሁሉ እናመስግን በፈተናችን ዋጋ በመከራችን ጸጋ እንድንቀበል እያሰብን ይህን እንጸልይ "ኦ እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ አአኩተከ በእንተ ኩሉ ግብር ዘአምጻእከ ላዕሌየ እመሂ ረኃበ አው ጽጋበ እመሂ ጥኢና አው ደዌ እመሂ ፍሰሐ አው ኃዘነ...ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በእኔ ላይ ስላመጣህብኝ ነገር ሁሉ አመሰግናለሁ ረሃብ ቢሆን፣ ጥጋብ ጤንነት ቢሆን፣ ደዌ ደስታም ቢሆን ኃዘን"( ሰይፈ ሥላሴ ዘሐሙስ)።
መስቀሉን የሚሸከም ምረረ ገኃነምን ጣዕመ መንግስተ ሰማያትን እየተዘከረ በመከራው ይደሰታል እንጂ አይማረርም። የጌታችን ወንድም የተሰኘ ራሱን የክርስቶስ ባርያ እያለ የጠራ ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ የመጀመርያ ምዕራፍ ቁጥር 2 እና 3 ላይ "ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት" ይለናል እኛም ከሐዋርያው ጋር እንዲህ እንላለን "ለእኛም ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ሥቃይ ምንም እንዳይደለ አስባለሁ።" (ሮሜ፣ 8:18)።
+++ ከፍኖተ መስቀሉ ከህያው ቅዱስ ቃሉ በረከት ይክፈለን። +++

Tuesday, 3 November 2015

‹‹ቅድስናን በገንዘብ?›› መጋቤ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ

አንድ አድርገን:

 መጋቤ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ   ዳላስ ውስጥ በነበረ አንድ ሀይማኖታዊ የምክክር መድረክ ላይ ዘመኑን የመሰሉ ጥያቄዎች ከአንዳንድ ወገኖች ቀርቦላቸው ነበር፤ ጥያቄ :- ( በዘመናችን ...