Monday, 9 November 2015

"ሉቃስ ከ12ቱ ሃዋርያት ሳይሆንቱ ከ72 አርድት ነው"

ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ
ጥቅምት 24 ቀን 2008 ዓ.ም ___በዲ/ን ኃይለ ማርያም አስፋው
ሉቃስ ማለት በላቲኑ ትርጓሜ ብርሃናማ፣ ብርሃን የያዘ ማለት ነው፡፡ በትርሜ ወንጌል የተሰጠው ትርጉም ደግሞ ሉቃስ ማለት ዓቃቤ ሥራይ (ባለ መድኃኒት) ማለት ነው፣ ቀድሞ ዓቃቤ ሥራይ ዘሥጋ (ሥጋዊ ሐኪም) ነበር በኋላ ግን ዓቃቤ ሥራይ ዘነፍስ ( መንፈሳዊ ሐኪም) ሆኖአልና፡፡ አንድም ተንሣኢ (ፈጣን) ማለት ነው ለስብከተ ወንጌል ይፋጠናልና፣ አንድም መበሥር (ብሥራ ነጋሪ) ማለት ነው ብሥራተ መልአክን ይጽፋልና በማለት ይተረጉመዋል፡፡የተወለደው በሶርያ አንጾኪያ ነው፡፡ የአሕዛብ ወገን የነበረና በኋላም ወደ ክርስትና እንደተመለሰ ታሪኩን የጻፉ ይናገራሉ፡፡ ቅዱስ ሉቃስ አይሁዳዊ ሳይሆን ወንጌልን የጻፈ ወንጌላዊ ነው፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ከሰባ ሁለቱ አርድዕት ነው የሚቆጠረው፡፡

ቅዱስ ሉቃስ የተወደደ ሐኪም ነበር፡፡ ለዚህም ማረጋገጫው ቅዱስ ጳውሎስ በቆላስይስ መልእክቱ ም.4፡14 የተወደደው ባለ መድኃኒቱ ሉቃስ ዴማስም ሰላምታ ያቀርቡላችኋልበማለት ገልጦታል፡፡ በወንጌሉም አጻጻፍ ላይ ስለ ሕመማቸውና ድኅነት ስለሚያገኙበት ሁኔታ ገልጦ ጽፏል፡- ስለ ደጉ ሳሚራዊ ሉቃ 10፡30-35፣ ደም ይፈሳት ስለነበረችው ሴት ሉቃ8፡43

ቅዱስ ሉቃስ ሠዓሊ ነበር፡፡ ይህ ሞያው ወንጌሉ ሲጽፍ ሥዕላዊና ገላጭ በሆነ መልኩ ለመጻፍ ረድቶታል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ትውፊት እንደሚናገረው የቅድስት ድንግል ማርያም ምስለ ፍቁር ወልዳ ለመጀመርያ ጊዜ የሳለው እርሱ ነው፡፡እነዚህም ሥዕሎች በኢትዮጵያ ውስጥ በተድባበ ማርያም' በደብረ ዘመዳ' በዋሸራ'በጅበላ ይገኛሉ፡፡

ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በሰዓታት ምስጋናው መልክአ ሥዕል ላይ ሰላም ለሥዕልኪ እንተ ሠዐላ በእዱ ሉቃስ ጠቢብ ዘእም ወንጌላውያን አሐዱ ከወንጌላውያን አንዱ የሆነው ጠቢቡ ሉቃስ ለሣላት ሥዕልሽ ሰላምታ ይገባል እያለ እመቤታችንን አመስግኖአታል፡፡

ቅዱስ ሉቃስ ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር የተገናኘው በአንጾኪያ ነው፡፡ ከዚያ በኃላ ተወዳጅ ደቀ መዝሙር ሆነ፡፡ በ2ኛ ጢሞ 4፡11 ሉቃስ ብቻ ከእኔ ጋር አለ፣ እንዲሁም ፊል 1፡24 ላይ አብረውኝም የሚሠሩ ማርቆስና አርስጥሮኮስ ዴማስም ሉቃስም ሰላምታ ያቀርቡልሃል ብሎ እንደገለጠው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ሰማዕትነት እስኪቀበል ድረስ ከርሱ ጋር እንደነበር በሐዋርያት ሥራ መጽሐፉ ገልጧል፡፡ ከቅዱስ ጳውሎስ በፊት የቅዱስ ዮሐንስ ደቀ መዝሙር እንደነበረ ትርጓሜ ወንጌል ላይ ለዮሐንስ ምድረ ፅርዕ ደረሰችው፣ ለሰብዓ አርድእት ግን ዕጣ የላቸውም፡፡ አንዱም ሁለቱም ሆነው አንዱን ሐዋርያ አንዱም ሁለቱም ሆነው አንዱን ሐዋርያ ተከትለው ይሄዳሉ ሉቃስም ዮሐንስን ተከትሎ ይሄዳል፡፡ መቄዶንያ የምትባል ሀገር ከፍሎ አስተምር ብሎ ሰጥቶታል፡፡

የሠለሥቱ ሐዲሳት መቅድም ደግሞ እንዲህ ይገልጠዋል ለሰብዓ አርድዕት ዕጻ የላቸውም አንዱም ሁለቱም አንዱን ሐዋርያ እየተከተሉ ይሄዳሉ ሉቃም ዮሐንስን ተከትሎ ሔዷል፣ ከሀገረ ስብከቱ ከፍሎ መቄዶንያ የምትባል ሀገር አስተምር ብሎ ሰጥቶታል፡፡ ከዚያ ገብቶ ጌታ ከፅንስ ጀምሮ ያስተማረውን ትምህርት የሠራውን ትሩፋት፣ ያደረገውን ተአምራት ቢነግራቸው ከገቢረ ኃጢያት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከአምልኮ ጣዖት ወደ አምልኮ እግዚአብሔር ተመለሱ አመኑ ተጠመቁ፡፡ ትምህርት ካልደረሰበት ለማዳረስ በሚሄድበት ጊዜ ታዖፊላ መኮንነ እስክንድርያ ይለዋል በርሱ ስብከት አምኖ ዜና ሐዋርያትን ጻፍልኝ ብሎት ጽፎለታል፡፡ አጻጻፉ አምስት ወገን ነው፤ ጌታ እንዳረገ መቶ ሃያው ቤተሰብ ባንድነት እንደ ነበሩ ይሁዳ እንደወጣ፣ በእግሩም ማትያስ እንደገባ፣ ባድነት ሳሉም መንፈስ ቅዱስ እንደ ወረደላቸው፣ በኢየሩሳሌም የነበሩ አይሁድ እስጢፋኖስን በድንጋይ ወግረው እንደገደሉት ይልቁንም መምህሩ ቅዱስ ጳውሎስ ከእምነት እስከ ሞቱ ያስተማረውን ትምህርት የሠራውን ትሩፋት ያደረገውን ተአምራት ጻፍልኝ ብሎት ጽፎለታል:: ጥቅምት 22 በሚነበበው ስንክሳር የቅዱስ ጴጥሮስም ደቀ መዝሙር እንደነበር ተገልጧል፡፡

ቅዱስ ሉቃስ ከሰማንያ አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሁለት መጻሕፍት አሉት፡፡ እነሱም የሉቃስ ወንጌልና የሐዋርያት ሥራ ናቸው፡፡ቅዱስ ወንጌሉን የጻፈው በአካይያ (በሮም 62-63 ዓ.ም ጻፈው የሚሉም አሉ) 58-60 ዓ.ም ሲሆን የጻፈበት ቋንቋ ፅርዕ ነው፡፡ የአጻጻፍ ስልቱ 'የትርጉም አጠቃቀሙ' የታሪክ ሂደቱ ሲታይ ቅዱስ ሉቃስ የተማረ ሊቅ እንደነበር ያስረዳል፡፡ ሲጽፍም የከበርህ ቴዎፍሎስ ሆይ፥ ከመጀመሪያው በዓይን ያዩትና የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት እንዳስተላለፉልን፥ በኛ ዘንድ ስለ ተፈጸመው ነገር ብዙዎች ታሪክን በየተራው ለማዘጋጀት ስለ ሞከሩ፥ እኔ ደግሞ ስለ ተማርኸው ቃል እርግጡን እንድታውቅ በጥንቃቄ ሁሉን ከመጀመሪያው ተከትዬ በየተራው ልጽፍልህ መልካም ሆኖ ታየኝ በማለት እርግጠኛ ሆኖ ነው፡፡ ይህ አገላለጡ ቅዱስ ሉቃስ የታሪክ ሰው ነበር ያሰኛል፡፡ ሁለቱንም መጻሕፍት ማለትም ወልጌሉንና የሐዋርያት ሥራ ራሱ እንደጻፈው በማያሻማ መልኩ በወንጌሉ መጨረሻና በሐዋርያት ሥራ መጀመርያ ላይ የተጠቀመው አገላለጽ በማየት መረዳት ይቻላል፡፡ ወንጌሉ በእርገት ሲጨርስ €™እስከ ቢታንያም አወጣቸው እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው፣ ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማይም ዐረገ። እነርሱም፤ ሰገዱለትና በብዙ ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፥ዘወትርም እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እየባረኩ በመቅደስ ኖሩ።ሉቃ 24፡50-53 በማለት ሲሆን የሐዋርያት ሥራ ሲጀምር ቴዎፍሎስ ሆይ፥ ኢየሱስ የመረጣቸውን ሐዋርያትን በመንፈስ ቅዱስ ካዘዛቸው በኋላ እስከ ዐረገበት ቀን ድረስ፥ ያደርገውና ያስተምረው ዘንድ ስለ ጀመረው ሁሉ መጀመሪያውን ነገር ጻፍሁ፤ደግሞ አርባ ቀን እየታያቸው ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት ነገር እየነገራቸው፥ በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለእነርሱ ራሱን አሳያቸው። ከእነርሱም ጋር አብሮ ሳለ ከኢየሩሳሌም
እንዳይወጡ አዘዛቸው፥ ነገር ግን። ከእኔ የሰማችሁትን አብ የሰጠውን የተስፋ ቃል ጠብቁ የሐ.ሥራ 1፡1-4 በማለት ነው፡፡

የቅዱስ ሉቃስ ወንጌል ከሦስቱ በተለየ መልኩ ታሪካዊና ስዕላዊ በሆነ መልኩ በተለይ ከአይሁድ ውጪ ያሉትና አሕዛብ ሊረዱት በሚችሉ መልኩ የተጻፈ ነው፡፡ በዘመኑ ከነበረው የአይሁድ ስለ ሴቶች ከነበራቸው አመለካከት ወጣ ባለ መልኩ ስለ ሴቶች አጉልቶ በስፋት የጻፈ ወልጌልዊ ነው ፡፡በተጨማሪም ስለ መንፈስ ቅዱስ ጸጋ፤ ስለ ጸሎት ፤ስለ ርኅራኄ ፤ስለ ሀብታምና ድሃ በሰፊው የጻፈ ወንጌላዊ ነው፡፡ በሐዋርያት ሥራ መጽሐፉ ስለ ቤተክርስቲያን' ስለ አንድነት' የሐዋርያነት መሠረት' ዓላማ' ትጋት' ማሸነፍ' ስለ ሌላው መጨነቅ' ኃላፊነትን ስለመወጣት'ተጋድሎን'በተግባር በሚታይና በሚጨበጥ ማስረጃ የጻፈ ሐዋርያ ነው፡፡

ቅዱስ ሉቃስ የሚመሰለው በገጸ ላህም ነው፡፡ምክንያቱም አምጽኡ ላሕመ መግዝዓ ወጥብሑ ንብላእ ወንትፌሣሕ ምስሌሁ (ፍሪዳ አምጡና እረዱ ከእርሱ ጋር እየበላን ደስ ይበለን) ሉቃ.15፤23 እያለ€™ ምሳሌውን ይጽፋልና፡፡ አንድም በጤግሮስ ይመሰላል ጤግሮስ ፈለገ መዓር (የመዓር ወንዝ) ነው ርስትነቱም ጸዊረ ነገር (ምሥጢር መሸከም) የሚቻላቸው ሰዎች ርስት ነው፡፡ ሉቃስም አባ ሥረይ ሎሙ እስመ በዘኢየአምሩ (አባት ሆይ የሚሠሩትን አያውቁምና ይቅር በላቸው) ይገብሩ' በትዕግሥትክሙ ታጠርይዋ ለነፍስክሙ (በመታገሳችሁ ነፍሳችሁን ገንዘብ ታደርጋላችሁ) እያለ ክቡድ ክቡድ ነገር ይጽፋልና፡፡

ቅዱስ ሉቃስ በድንግልና የኖረ ሐዋርያ ነው፡፡ በግሪክ ብዙ ሐዋርያዊ አገልግሎት ፈጽሟል፡፡ ያረፈውም በቆስጠንጢኖስ 2ኛ ዘመን በ84 ዓመቱ በሰማዕትነት ነው፡፡ ቅዱስ አጽሙ በ357 ወደ ቁስጥንጥንያ የፈለሰ ሲሆን ከቁስጥንጥንያ ወደ ጣልያን ፑዳ በ1177 ዓ.ም በድጋሚ ፈልሷል፡፡

ስለ እረፍቱም ጥቅምት 22 ቀን የሚነበበው ስንክሳር እንዲህ ይተርካል:: ቅዱሳን ጴጥሮስና ጳውሎስ ከተገደሉ በኋላ በሮም ሀገር የሚያስተምር ሆነ በቀናች ሃይማኖትም ይጸኑ ዘንድ ለምእመናን መልእክትን ይጽፍ ነበር ስለዚህም ጣዖት አምላኪዎች ከአይሁድ ጋር በመስማማት በአንድ ምክር ተስማሙ በንጉሥ ኔሮን ፊት ቆመው ስለ ሐዋርያው ሉቃስ እንዲህ ብለው ጮሁ ይህ ሉቃስ በሥራይ ብዙ ሰዎችን ወደ ትምህርቱ አስገባቸው አሉ፡፡ ንጉሥ ኔሮንም ወደ ፍርድ አደባባይ ሉቃስን እንዲያቀርቡት አዘዘ ሐዋርያው ሉቃስም ከዚህ ዓለም መውጫው እንደ ደረሰ በመንፈስ ቅዱስ አውቆ ወደ ባሕር ዳርቻ ሔደ በዚያም ዓሣ የሚያጠምድ አንድ ሽማግሌ ሰው አገኘ መጻሕፍቱንና ደብዳቤዎችን ሰጠው ወደ እግዚአብሔር መንገድ መርተው ያደርሱሀልና እሊህን መጻሕፍት ጠብቃቸው አለው፡፡ በንጉሥ ኔሮን ፊትም ቀርቦ በቆመ ጊዜ ንጉሡ በሥራይህ ሕዝቡን የምታስት እስከ መቼ ነው አለው ቅዱስ ሉቃም እኔ ለሕያው እግዚአብሔር ልጅ ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ነኝ እንጂ ሥራየኛ አይደለሁም ብሎ መለሰለት ንጉሥ ኔሮንም ሁለተኛ እንዲህ አለው እየጻፈች ሰዎችን የምታስት ይህች እጅህን እኔ እቆርጣታለሁ ይህንንም ብሎ የቀኝ እጁን እንዲቆርጡት አዘዘ፡፡ በቆረጡትም ጊዜ ንጉሥ ሆይ እኛ የዚህን ዓለም ሞት እንደማንፈራ ዕወቅ ነገር ግን የጌታዬና የፈጣሪዬን ኃይሉን ታውቅ ዘንድ አሳይሃለሁ ይህንንም ብሎ የተቆረጠች የቀኝ እጁን በግራ እጁ አንስቶ ከተቆረጠችበት ቦታዋ ላይ አገናኝቶ እንደ ቀድሞዋ ደኅነኛ አደረጋት ከዚህም በኃላ ለያት በዚያም የነበሩ አደነቁ የሠራዊቱም አለቃና ሚስቱ ብዙዎችም ሰዎች ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ቁጥራቸውም አራት መቶ ሰባ ሰባት ነፍስ ሆነ፡፡ ንጉሡም ከቅዱስ ሉቃስ ጋር ራሶቻቸውን እንዲቆርጡ አዘዘና ቆረጡአቸው የምስክርነት አ
ክሊልም በመንግስተ ሰማያት ተቀበሉ ከዚህም በኋላ የቅዱስ ሉቃስን ሥጋ በማቅ አይበት ውስጥ አድርገው ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ ወደ አንድ ደሴት ደረሰ ምእመናንም አግኝተው ወስደው ገነዙት በአማረ ቦታም አኖሩት ለእግዚአብሔር ምስጋነና ይሁን እኛንም በዚህ ሐዋርያ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡

ሰላም ለሉቃስ እንተ ረትዐ ልሳኑ ወንጌለ መለኮት ይጽሐፍ እምእለ ብዙኃን ወጠኑ፡፡ ከመ ያርኢ ኀይለ ቅድመ ኔሮን ወተዐይኑ አስተላጸቃ ወሌለያ የማኑ ለምትርት እስመ ላዕሌሁ ተሠውጠ ለክርስቶስ ሥልጣኑ፡፡

No comments:

Post a Comment